Friday, November 2, 2012

ሰበር ዜና፡ በስደት የሚገኘውና በሃገር ቤት የሚገኘው ሲኖዶስ ውሳኔ አሳለፉ !

 በስደት የሚገኘው ሕጋዊው ሲኖዶስ ጉባኤውን በኦሃዮ ከተማ ጀመረ። ትናንት በጸሎት ተከፍቶ የነበረው ይሄው ታሪካዊው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ እስከፊታችን ቅዳሜ ኖቬምበር 3 ቀን 2012 ዓ.ም እንደሚቀጥል በስፍራው የሚገኙት የዘ- ሐበሻ ድረ ገጽ ምንጮች ዘገቡ። 

ዛሬ ኦክቶበር 31 ቀን 2012 በስደት የሚገኙ በርከት ያሉ ጳጳሳት እንዲሁም ከወትሮ በተለየ መልኩ ብዛት ያላቸው ካህናት በተገኙበት በኦሃዮ ከተማ በተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ዓመታዊ ጉባኤ ላይ በዋነኝነት የተነሳው አጀንዳ ከሃገር ቤቱ ሲኖዶስ ጋር ስለሚደረገው ድርድር እና ብጹዕ አቡነ መርቆርዮስ የፓትርያርክነታቸውን ስፍራ በኢትዮጵያ ስለሚረከቡበት ሁኔታና በተዛማጅ ጉዳዮች ዙሪያ ነበር።


በዚህ አጀንዳ ላይ ሲኖዶሱ ከፍተኛ የሆነ ውይይት ማድረጉን የገለጹት የዘ-ሐበሻ የቅዱስ ሲኖዶስ ምንጮች ከሕዳር 26 ቀን 2012 – ህዳር 30 ቀን 2012 በዳላስ ከተማ በሚደረገው የሁለቱ ሲኖዶሶች ድርድር ላይ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ፣ በሃገር ቤቱ ሲኖዶስ የቤተክርስቲያን የበላይ ጠባቂ እንዲሆኑ የተቀመጠውን ቅድመ ሁኔታ እንደማይቀበለውና ፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ ከነክብራቸውና ስማቸው የፕትርክናውን ቦታ እንዲቀበሉ የሚል አቋም ይዞ ወደ ድርድር እንዲገባ ውሳኔ ተላልፏል።


ከዚህ ቀደም ከሃገር ቤቱ ሲኖዶስ ጋር ድርድር ሲደረግ የሕጋዊውን ሲኖዶስ ወክለው ለድርድር የቀረቡት፣ አቡነ ኤልያስ፣አቡነ መልኬጼዲቅ፣ ሊቀካህናት ምሳሌና ቄስ ገዛኸኝ እንደነበሩ ያስታወሰው ምንጫችን በዛሬው ጉባኤ ላይ ሲኖዶሱን ወክለው የሚደራደሩት አባቶች ላይ ለውጥ ተደርጓል። አቡነ ኤልያስ፣ አቡነ መልኬጼዲቅና ሊቀ ካህናት ምሳሌና የለንደኑ አቡነ ጎርጎርዮስ በሕዳር ወር ላይ ለድርድር ወደ ዳላስ እንዲሄዱ ተመርጠዋል ያለው ምንጫችን ለረዥም ጊዜ በድርድሩ ውስጥ የነበሩት ቄስ ገዛኸኝ ለምን በአቡነ ጎርጎርዮስ ሊተኩ እንደቻሉ ያደረሰን መረጃ የለም።


የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነገም ቀጥሎ የሚውል ሲሆን ዘ-ሐበሻ ተጨማሪ መረጃዎችን ተከታትላ ታቀርባለች።ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ በተገኙበት ኦሃዮ የተጀመረው ጉባኤ የ2ኛ ቀን ውሎ ይሄን ሲመስል በአዲስ አበባ ዛሬ ጉባኤውን ያካሄደው የሃገር ቤቱ ሲኖዶስ ያስተላለፈው ውሳኔ በሁለቱ ሲኖዶስ እርቅ ዙሪያ ተስፋ የጣሉ ወገኖችን ተስፋ አስቆርጧል። ከደጀ ሰላም ድረ ገጽ ያገኘነውን መረጃ እንደሚከተለው እንደወረደ አስተናግደነዋል።


የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ “ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ እያለ ራሱን የሚጠራው” የሚለው የቅዱስ ሲኖዶሱ መግለጫ ተ.ቁ (2) “እኛንም አላስደሰተንም፤ እንዲስተካከል እናደርጋለን” ሲሉ ሌላው የቅዱስ ሲኖዶሱ አባል ደግሞ እንዲህ ያለው ቃል ከጋዜጠኞች በፊት ምልአተ ጉባኤው በተናበበው የመግለጫው ክፍል ላይ እንዳልነበረ ተናግረዋል፤“ስድስተኛውን ፓትርያርክ በመንበሩ ላይ ለማስቀመጥ እየተዘጋጀን ነው ያለነው፤ ሕጉን ካጸደቅን በኋላ ወደ ምርጫው ነው የምንገባው፤ በውጭም ያሉት ተቀብለውን፣ በውስጥም ያለነው ተቀብለናቸው ከእኛው ጋራ ምርጫውን እንዲያካሂዱ ፈቃደኞች ነን፡፡” /ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል/“ጳጳስ ንብረት የለውም – ጎመን የሚዘራበት፣ ሽንኵርት የሚተክልበት፤ ንብረቶቹ ምእመናን ናቸው፡፡” /ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል በሕገ ቤተ ክርስቲያን ማሻሻያው ላይ ከጋዜጠኞች ለቀረቡላቸው ጥያቄ የመለሱት/በአዲስ አበባ አራት አህጉረ ስብከት አደረጃጀት ሂደት ከሥራ አስኪያጅነት የሚወገዱት ንቡረእድ ኤልያስ በጸሐፊነት ከያዙት የዕርቀ ሰላሙ ልኡክ አባልነትም እንዲወጡ መደረጋቸው ተሰምቷል፡፡


የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በ2000 ዓ.ም ያጸደቀው “የማዕርገ ክህነት አሰጣጥ፣ ሥርዐተ ምንኵስናን፣የካህናትና መነኰሳት የማዕርግ አለባበስ ደንብ” አፈጻጸም ጥብቅ ቁጥጥር እንዲደረግበት ትእዛዝ ሰጠ፡፡ 


የደንቡን ሙሉ ይዘት እናቀርባለን፡፡ የምንኵስና ልብስ ለብሰው ሕዝቡን በማታለልና ሃይማኖታችንን በማስነቀፍ ላይ ከተሰማሩ ምግባረ ብልሹ የስም መነኰሳት ነን ባዮች ሕዝበ ክርስቲያኑ ራሱን ነቅቶ እንዲከላከልና መንግሥትም የሕግ ከለላ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ጠይቋል “ሀገረ ስብከትዎን አያውቁትም” በሚል በምልአተ ጉባኤው የተወቀሱትና የምእመናን አቤቱታ የበረታባቸው ብፁዕ አቡነ ገሪማ ከድሬዳዋ ሀ/ስብከት ተነሥተው ብፁዕ አቡነ ዕንባቆም ተመድበዋል፤ ብፁዕነታቸው የምዕራብ ሐረርጌ ሀ/ስብከትን ደርበው ይመራሉ፤ ብፁዕ አቡነ ዕንባቆም የለቀቁት ደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በጋሞጎፋው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ ይመራል፡፡ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የውጭ ግንኙነት መምሪያን በበላይ ሓላፊነት እንደያዙ የካራ መድኃኔዓለም እና አቡነ ገሪማ ገዳም የበላይ ጠባቂ ኾነዋል፡፡

የመንበረ ፓትርያርካችን የጋዜጣዊ መግለጫ ዝግጅትና የጋዜጣዊ ጉባኤ ሥነ ሥርዐት የቤተ ክርስቲያናችንን ከፍተኛ አመራር የሚያስከበር መኾን እንደሚገባው ተተችቷል፤የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት የቅዱስ ሲኖዶሱን የምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ዘገባ ያስተላለፈበት ሰዓትና አዘጋገብ ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የተሰማቸውን ቅሬታ በጋዜጠኞች ፊት አሰምተዋል፡፡ 


ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ጣቢያው የምልአተ ጉባኤውን መክፈቻ “ሰው ከተኛ በኋላ ምሽት አራት ሰዓት ላይ መተላለፉ ሰዉ እንዳያየው ነው ወይ? የሰማነውስ ነገር እኛ ያልነውን ነገር በትክክል ገልጧል ወይ?” የሚል ጥያቄ አቅርበዋል፤“የብፁዕነታቸው ቅሬታ የሁሉም አባቶች ሐሳብ ነው” ያሉት ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል በበኩላቸው ቅዱስ ሲኖዶሱ በዘገባውና አዘጋገቡ ላይ የወሰደውን ትዝብትና የተሰማውን ቅሬታ በመደበኛ ኹኔታ ለሚመለከታቸው የጣቢያው የሥራ ሓላፊዎች እንደሚያቀርብ አስታውቀዋል፡፡ (ደጀ ሰላም፤ ጥቅምት 21/2005 ዓ.ም፤ ኦክቶ. 31/2012)፦ አርባ ያህል ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ለዐሥር ቀናት ሲመክሩበት የሰነበቱበት የጥቅምት 2005 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ ረፋድ ላይ ተጠናቋል፡፡ 

ምልአተ ጉባኤው ያዘጋጀው 17 ነጥቦችን የያዘው ጋዜጣዊ መግለጫ በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ አማካይነት በቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለመግለጫው በተጠሩት የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ብዙኀን መገናኛ ጋዜጠኞች ፊት በንባብ ተደምጧል፡፡ ከዚህ በኋላ በተለየ ክፍል በተከናወነው ጋዜጣዊ ጉባኤ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ከተወሰኑ ጋዜጠኞች ለተነሡ ጥቂት ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ጥያቄዎቹ ከመግለጫው አጻጻፍ ጀምሮ በዕርቀ ሰላሙ ሂደት እና በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ዕጣ ፈንታ፤የፓትርያርክ ምርጫ ሕጉን ሕገ ፓትርያርክን ፓትርያርኩ ሳይኖር ስለምን ለማሻሻል እንደተፈለገ፤ የጳጳሳት ድርብ ዜግነት፣ ንብረት ማፍራትና ውርስ ጉዳይ በሚሻሻለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ስለሚታይበት ኹኔታ፤ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለአራት አህጉረ ስብከት እንዲከፈል ስለተወሰነበት ወቅትና ኹኔታ የተመለከቱት ነጥቦች ይገኙባቸዋል፡፡


ብፁዕነታቸው ለጋዜጣዊ ጉባኤ ካላቸው አዲስነት ጋራ የአነጋገራቸው ለዛና ቀጥተኝነትም የጋዜጠኞችን ቀልብ የሳበ ሲሆን ምላሾቹ ግን ጥቂት የማይባሉትን መኮርኮሩ፣ በአንዳንዶቹም ዘንድ ስጋት መፍጠሩ አልቀረም፡፡ “ችግር በገጠመ ጊዜ አገርን ለቀቅ አድርጎ ጎረቤት አገር መኖር ይቻላል፤ አገርን ከለቀቁ በኋላ ሲኖዶስ በሚል ማቋቋም፣ ሲኖዶስ የሚለውን ቃል መጠቀም አግባብ አልነበረም፤ ሲኖዶስ አንድ ነው፤ አይከፈልም፤ መንበሩ ያለው እዚህ ነው አይሰደድም፤ እዚያ ያለው ጥገኛ ነው” ያሉት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል÷ ዕርቀ ሰላሙን በተመለከተ “ስንጻጻፍ፣ ሰውም ሲላክ ቆይቷል፤ እግዚአብሔር ባለው ጊዜ ይፈጸማል” ብለዋል፡፡


የዕርቁ ሂደት ከፓትርያርክ ምርጫው ጋራ ስላለው ግንኙነትም “ኻያ ዓመት ሙሉ አምስተኛ ፓትርያርክ እያልን ቆይተን ወደ አራተኛ አንመለስም፤ ስድስተኛውን ፓትርያርክ በመንበሩ ላይ ለማስቀመጥ በዝግጅት ላይ ነው ያለነው፤ ሕጉን ካጸደቅን በኋላ ወደ ምርጫው ነው የምንገባው፡፡ ቅዱስነታቸው አቡነ መርቆሬዎስ ከፈለጉ እዚሁ እኛው ግቢ ማረፊያ ተሰጥቷቸው፣ ካልፈለጉም በመረጡት ገዳም አስፈላጊው ነገር ተሰጥቷቸው በጸሎት ተወስነው ሊቀመጡ ይችላሉ፤ እዚያ ያሉት እዚህ የተሾሙትን ተቀብለው፣ እዚህ ያለነውም እዚያ የተሾሙትን ተቀብለን ከእኛው ጋራ ምርጫውን ለማካሄድ ፈቃደኞች ነን፡፡”


ብለዋል። “ሃይማኖት እንጂ ሕግ በየጊዜው ወቅቱን ተመልክቶ የሚሻሻል ነው” ያሉት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ለሥራ አመቺ ተደርጎ፣ የሚጨመር ካለ ተጨምሮ፣ የማያስኬድ ነገር ካለ እንዲያስኬድ ኾኖ እንደሚሻሻል ገልጸዋል፡፡ ዋና ጸሐፊው አያይዘውም በፍትሐ ነገሥቱ ለሁሉም ለየራሱ የተደነገገለት ተልእኮ (ድርሻ) መኖሩን በማስታወስ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ማሻሻያ “ለፓትርያርክ የሚገባው ድርሻ አይነካበትም” ብለዋል፤ የፓትርያርክ ምርጫ ሕጉም ስለ አመራረጡ፣ ስለ አካሄዱ በመኾኑ ፓትርያርኩ አለመኖሩ የሚያሰጠው የተለየ ትርጉም እንደሌለ አስረድተዋል፡፡


ስለ ጳጳሳት ንብረት ማፍራትና ውርስ ጉዳይ ለተነሣው ጥያቄ ብፁዕነታቸው በጥቅሉ “ጳጳስ ንብረት የለውም፤ እርሻ አያርስም፤ ጎመን አይዘራም፤ ሽንኵርት አይተክልም፤ ንብረቶቹ እናንተ ምእመናን ናችኹ” በማለት መልሰዋል፡፡ በአገራችን ሕግ ስለ ድርብ ዜግነት የተደነገገውን በመጥቀስ የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው ‹ኢትዮጵያውን› ጳጳሳት ስለመኖራቸው ለቀረበላቸው ጥያቄም “አዎ፣ የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው ጳጳሳት አሉ” ካሉ በኋላ በሚሻሻለው ሕግ ኢትዮጵያዊ ብቻ እንዲኾኑ ከሚያስፈልገው አኳያ ጥያቄውን እንደ ጥቆማ በመውሰድ ቅዱስ ሲኖዶሱ እንደሚመክርበት አመልክተዋል፡፡


በአጠቃላይ አጋጣሚው ቤተ ክርስቲያናችን የብዙኀን መገናኛዎችን፣ ከቤተ ክህነቱ አስተዳደር ጋራ በተያያዘ የታሪክ እና ፖሊቲካ ተንታኞችን ቀልብ ይዛ ባለችበት ወቅት ስለ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውሳኔዎች የሚሰጡ ጋዜጣዊ መግለጫዎችና የሚዘጋጁ ጋዜጣዊ ጉባኤዎች መድረኩ የሚፈጥረውን ዕድል ሁሉ አሟጠው የሚጠቀሙ፣ በባለሞያ የታገዘ ከፍተኛ ዝግጅት ሊደረግባቸው እንደሚገባ ዛሬ የታየው የዜና ሰዎች ትኩረት እና ብዛት ግድ እንደሚለን ሊጤን ይገባል እንላለን፡፡ ለበለጠ ትንታኔ እዚህ ይጫኑ


No comments:

Post a Comment