Saturday, January 25, 2020

የአማራ ክልል ፈተናዎች እና “ጭምት” አመራሩ – ክፍል ሁለት (በመስከረም አበራ)



በሃገራችን ሩብ ምዕተ-ዓመት ያስቆጠረውን የህወሃት የበላይነት ያስወገደውን ለውጥ ተከትሎ የአማራ ክልል አዳዲስ ፈተናዎች እንደተጋረጡበት ባለፈው ሳምንት ባስነበብኩት ፅሁፍ ለመዳሰስ ሞክሬያለሁ፡፡እነዚህ ፈተናዎች በህወሃት የበላይነት ዘመን ለአማራ ህዝብ ላይ ተጋርጠው በነበሩት ፈተናዎች ላይ የተደረቡ መሆናቸው ፈተናውን ድርብርብ እና ውስብስብ ያደርገዋል፡፡የመጣው ለውጥ የአማራን ህዝብ የቆዩ ፈተናዎች በማቃለል ረገድ ያመጣው ተጨባጭ ነገር አለ ብሎ ለመናገር አያስደፍርም፡፡በአማራ ህዝብ ላይ የተቃጣው ጥቃት ኢትዮጵያን ለማጥፋት የተወረወረው ፋላፃ አካል ነው፡፡በአማራ ክልል ላይ የፈተና ዶፍ የሚያወርዱ አካላት ኢትዮጵያን እና አፈጣጠሯን የማይወዱ የፖለቲካ ሃይሎች ናቸው፡፡ይህን የደደረ ፈተና ለማቃለል ደግሞ የፈተናውን  ክብደት የሚመጥን ንቁ፣ቆራጥ፣ጥንቁቅ እና የተሰጠ አመራር ያስፈልጋል፡፡ሆኖም አማራ ክልልን የሚመሩ አመራሮች ወቅቱ የሚጠይቀውን የአመራር አቋም ይዘው ስለመገኘታቸው አፍ ሞልቶ የሚያስወራ ምልክት ያለ አይመስልም፡፡
የአማራ ክልል አስተዳዳሪዎች በህዝባቸው ልብ የሚጣልባቸው እንዳይሆኑ ያደረገ በርካታ ምክንያት አለ፡፡ የመጀመሪያው የጥራዝ ነጠቁ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ትግል የአማራን ህዝብ በጨቋኝት የፈረጀበት ደመ-ነፍሳዊ አካሄድ የወለደው አማራውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ መርገም ሁሉ ምንጭ አድርጎ የማየቱ ትንተና ያመጣው ነገር ነው፡፡ ይህ አማራውን ጨቋኝ አድርጎ የማየቱ ነገር ህወሃት የተባለው የባሰበት ጥራዝ ነጠቅ ደደቢት ከመሸገበት፣ አዲስ አበባ እስከ ገባበት፣ ከዛም ፈላጭ ቆራጭ ሆኖ ግማሽ ምዕተ አመት ስልጣን ላይ በተወዘተበት ዘመን ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ህወሃት ጌታ ሆኖ ኢትዮጵያን ሲያሾር በኖረበት ዘመን ካሰማራቸው ሶስት የእህት አምስት የአጋር ድርጅት ሎሌዎች መሃል አንዱ የአማራ ክልልን የሚያስተዳደርው ብአዴን ነበር፡፡
ሁሉም የአባል/አጋር ፓርቲ ሎሌዎች በአሳዛኝ ራስን የማከራየት ጎስቋላ ህይወት ውስጥ የነበሩ ቢሆኑም የብአዴንን ለየት የሚያደርገው በራሱ ህዝብ ላይ የተቃጣውን ጦርነት ሊያጋፍር የወጣ ሎሌ መሆኑ ነው፡፡ይህ ቡድን ከሎሌነቱ የባሰ ሌላ ፈተና ነበረበት፡፡ ይኽውም “እንደ ወጣበት ህዝብ ትምክህተኛ አለመሆኑን” ለጌታ ህወሃት የማስመስከር የማያልቅ ስራ ነበር፡፡ይህን ለማስመከር ደግሞ ህወሃት በአማራ ህዝብ ላይ የሚያወርደውን ሁለንተናዊ መከራ ዝቅ ሲል ባላየ ማለፍ ከፍ ሲል ደግሞ ከህወሃት ጋር ተደርቦ የራስን ህዝብ ልብስ አስወልቆ በእሾህ ለበቅ መለብለብ ያስፈልግ ነበር፡፡ይህን በማድረግ የብዴን ሹማንነት “አማራ በመሆናቸው ምክንያት ከዘር የወረሱትን  የትምክህተኝነት ሃጢያት” የማራገፋቸውን ለጌታ ህወሃት ያስመሰክሩ ነበር፡፡ይህ ከሩብ ምዕተ-ዓመት በላይ ከብአዴን ሹማምንት ጋር አብሮ የኖረ አባዜ እንዲህ  በቀላሉ ትቷቸው ሊሄድ አይችልምና ዛሬም ለህዝባቸው ለመቆም ወገባቸውን ሳይዘው አልቀረም፡፡
ይህ ድክመት ከብአዴን ሹማንምንት ያለፈ ታሪክ ብቻ የሚቀዳ አይደለም፡፡ይልቅስ ከላይ ከፍ ብሎ እንደተቀመጠው ከነጥቆ በረሩ የኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ ዘመን ጀምሮ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ንፋስ ውስጥ አማራውን ጨቋኝ አድርጎ የመሳሉ ነገር ዛሬ ድረስ ተሻግሮ ክልሉን የሚመሩ ባለስልጣናት ለህዝባቸው እንዳይሰሩ ቀላል የማይባል ተፅዕኖ ሳያስከትል አልቀረም፡፡ይህም ማለት የአማራ ክልልን የሚመሩ ባለስልጣናት ለህዝባቸው የመቆርቆር ነገር ካሳዩ “የቆየ ትምክህታቸውን ሊመልሱ፣የቀድሞውን ስርዓት ሊያመጡ” የሚል ዜማ ይከተላቸዋል፡፡ ይህ ነገር የአማራ ክልል አመራሮች ከሌላው በተለየ “ጭምት” እንዲሆኑ ሳያደርግ አልቀረም፡፡ይህን ነገር ለመስበር ደግሞ የክልሉ አመራሮች በህወሃት ዘመን በከፍተኛ የስነልቦና ስልበት ውስጥ የቆዩ በመሆናቸው ዛሬ ብድግ ብለው በራሱ የሚተማመን፣የሚቆምለት መርህ ያለው፣የፖለቲካ ተደራዳሪነትን ካርዶችን አሰላስሎ ሰብስቦ አጀንዳ አስቀማጭ ሊሆኑ አይችሉም-በጥብቅ ሰንሰለት ታስሮ የኖረ ምርኮኛ ሰንሰለቱ ቢፈታለትም ቶሎ እጁን ማዘዝ እንደማይችል ሁሉ!
ይህ ልማድ ግን ለአማራ ህዝብ ደህንነትም ሆነ ለኢትዮጵያ ህልውና ሲባል ነገ ዛሬ ሳይባል መወገድ ያለበት ልማድ ነው፡፡አማራ ክልልን የሚመሩ መሪዎች “ጭምትነታቸውን” ማቆም አለባቸው፡፡በክልሉ ላይ የተደቀነው ፈተና በትናንቱ የፖለቲካ ልማድ የሚወጡት አይደለም፤ለአፍታም የሚያስተኛ አይደለምና ወገብ ጠበቅ አድርጎ መስራት ያስፈልጋል፡፡ እዚህ ላይ “የሚሰራው ስራ ምንድን ነው?” የሚል ተገቢ ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡የሚሰራው በርካታ ስራ ቢሆንም እኔ የታየኝን ላስቀምጥ፡፡
ነቀፌታን ማስወገድ
ለውጥ መጣ ከተባለ ወዲህ በተለይ ወያኔ እንኳን ወደመረሻው አካባቢ ረስቶት የነበረውን የአማራን ህዝብ የማብጠልጠል ነገር በተለይ በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ በግልፅ በአደባባይ እየተቀነቀነ ይገኛል፡፡ይህ የአማራን ህዝብ የማብጠልጠያው መግቢያ በር “ነፍጠኛ” የሚለው አማራው ሊያፍርበት የማይችለው፣ይልቅስ የሚኮራበት ስም ነው፡፡ሆኖም ዋናው ጉዳይ ያለው አማራው “ነፍጠኛ” ለሚለው ስም  የሚሰጠው ትርጉም ላይ አይደለም፡፡ዋናው ጉዳይ ያለው ሌሎች ለዚህ ስም የሚሰጡት ትርጉም ላይ ነው፡፡ የመከፋፈል ካህኑ መለስ ዜናዊ “ነፍጠኛ” የሚለውን ቃል አማራው ከሚያውቀው በተለየ ሁኔታ ለካድሬዎቹ ሲያሰለጥን ኖሯል፡፡አማራውን ከኢትዮጵያ እኩል የሚጠሉ አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞችም ሆኑ የሌላ ዘውግ ፖለቲከኞች “ነፍጠኛ” ለሚለው ስም ያላቸው ትርጓሜ ከመለስ ዜናዊ ጥራዝ ነጠቅ ካድሬዎች የተለየ አይደለም፡፡
በነዚህ አካላት ትርጉም “ነፍጠኛ” ማለት ቅኝ ገዥ፣የሰው ባህል ጨፍላቂ፣የሰው መሬት ቀማኛ፣በኢትዮጵያ ብሄረሰቦች ላይ የዘር ማጥፋት ያደረገ ጨካኝ ማለት ነው፡፡በዚህ እሳቤ መሰረት አሁን በህይወት ያሉ፣ የዚህ ነፍጠኛ የተባለው “ጭራቅ” ልጆች ደግሞ አሁን ላይ የአባቶቻቸውን ሃጢያት ደሞዝ ማግኘት አለባቸው የሚል የማይናወጥ አቋም አለ፡፡ይህ እሳቤ ነው በኢትዮጵያ ዳርቻ ላሉ አማሮች በህይወት የመኖር ስጋት፣ይህ እሳቤ ነው አማራ ክልልን በየአጋጣሚው የማሳቀል ምክንያት፣ይህ እይታ ነው ጊዜ እና ቦታ ሳያስመርጥ ከባስልጣን እስከ መደዴ የፖለቲካ ንግግር ማሳመሪያው አማራን ማንጓጠጥ አድርጎ እንዲታሰብ ያደረገው፡፡ችግሩ አማራውን በማንጓጠጥ የሚቆም ቢሆን ኖሮ በአመዛኙ  የአማራ ህዝብ ካለው ጠንካራ የስነልቦና ውቅር አንፃር አሳሳቢ አይሆንም ነበር፡፡ ዋናው ችግር ይህ እሳቤ ወደ ተግባር ተቀይሮ እጅ እና እግር፣ጥፍር እና ጥርስ አውጥቶ አማራውን እና የአማራ የተባለን ነገር ሁሉ ሊውጥ መንደርደሩ ነው፡፡ይህ አደጋ በቀጥተኛ ቋንቋ ሲገለፅ ከክልሉ ውጭ የሚኖረው አማራ በተለይ በከፍተኛ የእልቂት ስጋት ውስጥ መገኘቱ ነው፡፡
ይህን ችግር ለማቃለል ክልሉን ከሚመሩት መኳንንት የቀረበ ሰው የለም፡፡ችግሩን ለማቃለል በክልሉ ሹማንት ሊደረግ የሚገባው ቀዳሚው ነገር ከክልሉ ውጭ ለሚኖረው አማራ ሃላፊነት ያለባቸው መሆኑን መረዳት ነው፡፡ይህን ከተረዱ በኋላ በመጀመሪያ ከእራሳቸው ፓርቲ ጓዶች የሚመጣውን እልቂት የሚጠራ የአደባባይ ንግግር በአንክሮ ተመልክቶ በጠንካራ ወገብ መፋለም ነው፡፡ይህ ማለት አንድ ሁለት ቀን ተደርጎ የሚረሳ የሁለት ካድሬዎች የፌስ ቡክ ንትርክ ማለት አይደለም፡፡ከዛ ያለፈ ነገር ያስፈልጋል፡፡ባለቤት ካልናቁ አጥር አይነቀነቅምና “በአንድ ፓርቲ ጥላስር ያለ አጋር ተዝናንትቶ በአደባባይ የምመራውን ህዝብ የሚወርፈው እኔን እንዴት ቢያየኝ ነው?” ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፤በግማሽ አይን መታየት ጥሩ ነገር አለመሆኑን ለራስ መንገር ያስፈልጋል፣መከባበር የሌለበት የሽንፈት ህብረት ወንዝ እንደማያሸግር አምኖ ለዚሁ መስራት ያስፈልጋል፡፡ ይህን ገቢራዊ ለማድረግ በፓርቲ ስብሰባዎች፣በፖለቲካዊ ግንኙነቶች ወቅት አጥንት ለብሶ መቆምን ይጠይቃል፡፡
የቤትን እርግጫ አደብ ካስያዙ በኋላ የሚቀጥለው ከወጭ የሚመጣውን ውረፋ መቋቋም ነው፡፡ከውጭ የሚመጣው ውረፋ ከዘውግ ብሄርተኞች የሚሰነዘር የአማራውን ህዝብ ህይወት እጅግ ለከፋ አደጋ የሚያጋልጥ፣የማምለክ መብቱን የሚጥስ በአጠቃላይ አማራነትን የሞት ምልክት የሚያደርግ እጅግ አደገኛ ነገር እየሆነ መጥቷል፡፡ይህን ነገር ዝም ብሎ ማየት የአማራ ህዝብ ፍትህን ከእጁ እንዲያገኝ መገፋፋት፣ሃገራችንንም ወደ አላስፈላጊ ትርምስ መክተት ነው፡፡ቤኒሻንጉል ላይ የአማራ ህፃናት ሳይቀሩ በቀስት ሲሰነጠቁ ክልሉን የሚመራው አመራር ችላ በማለቱ የሆነው ነገር የሚታወቅ ነው፡፡ያን መሰል ድርጊት አሁንም እንዳይደገም መፍትሄውን ማምጣት የሚችለው መራሩ ነው፡፡መፍትሔ ማምጣት ማለት ደግሞ ህፃን ልጅን እንኳን የማያሳምን “እየተከታተልን ነው፣ጎጅ ባህል ስለሆነ ነው፣እልባት ለመስጠት አቅጣጫ ተቀምጧል” የሚል አሰልች ፕሮፖጋንዳ መደርደር አይደለም፡፡የአማራ ህዝብ በሚገደልበት ክልል ሁሉ ክልሉን የሚመሩ ባለስልጣናት ችልታ ወይ እገዛ አብሮ አለ፡፡ይህ ቅድም ከላይ የተነሳው መለስ ዜናዊ በካድሬዎቹ ውስጥ አስርጎት የሄደው ስልጠና ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ አማራው በሚታረድበት ጥጋጥግ ያሉ አመራሮች ሁሉ ሃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው የሚጠየቁበትን መንገድ ጠንከር ብሎ መጠየቅ የአማራ መኳንንት ፋንታ ነው፡፡በየሚያስተዳድሩት ክልል  አማሮች ሲታረዱ፣ቤታቸው ሲቃጠል፣እምነት ቦታቸው ዶግ አመድ ሲሆን ዝም የሚሉ በብልፅግና ፓርቲ ስር ያሉ አመራሮች አማራ የክልልን ከሚመሩ ጓዶቻቸው ይልቅ ለነጃዋር የሚቀርብ ስነ-ልቦና ያላቸው እንደማይጠፉ ግልፅ ነው፡፡እነዚህን አመራሮች ተከታትሎ መገዳደር የአማራ መኳንንት ስራ ነው፡፡በአጠቃላይ የአማራ ህዝብ ስቃይ ነፍጠኛ የሚለውን ስም እና ተከትሎት የሚመጣውን እሳቤ ተንተርሶ የሚመጣ ነውና ይህን የነቀፌታ እሳቤ በአደባባይ ማፀባረቅ ቀለል ተብሎ የሚነገር መሆኑን ማስቆም ግድ ነው፡፡ሌሎች ብሄረሰቦች ሊባሉ የማይፈልጉትን ስም ማስወገድ የቻሉት ወከልናችሁ የሚሏቸው ልጆቻቸው ተግተው ስለሰሩ ነው፡፡ “ለሌሎች ህዝቦች የሚደረገው ጥንቃቄ ለእኔ ህዝብ የማይደረገው እኔ ምን ቢጎድለኝ ነው?” ብሎ ማሰብ ከባድ ነገር አይደለም!
ራስን በትክክል መግለፅ
የዘውግ ፖለቲከኞች የአማራን ክልልን በውስጡ ያሉ ብሄረሰቦችን መብት ካለማክበር እስከ ዘር ማጥፋት ወንጀል መፈፀም ድረስ በደረሰ የበሬ ወለደ ክስ እንደሚያብጠለጥሉ የሚታወቅ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ለዚህ ዘመቻ ምንም የሚመልሰው ነገር ስለሌለ የሃሰት ክሱ የብቸኛ እውነትነትን ማማ ተቆናጦ ቁጭ ብሏል፡፡ ዛሬ አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያውቀው የቅማንት ህዝብ በህገመግስቱ በተደነገገው መሰረት  ብሄረሰብ የሚያስብለው የተለየ ቋንቋ ሳይናገር፣ አማርኛ እየተናገረ የልዩ ብሄረሰብ አስተዳደር የተሰጠው ብቸኛ ህዝብ መሆኑን ሳይሆን ጥያቄው ታፍኖ በአማራ ልዩ ሃይል የዘር ማጥፋት እየተደረገበት እንደሆነ ነው፡፡ይህን የሚያራግበውን ሚዲያ በህግ ተጠያቂ ማድረግ ቀርቶ የተለያዩ ሚዲያዎችን ተጠቅሞ የአማራ ክልል ለቅማነት ህዝብ ያደረገውን እላፊ መብት የማክበር ፈለግ የማስተዋወቅ ስራ እንኳን መስራት አልተቻለም፡፡ ስለዚህ ሃሰቱ እውነት አክሎ በአማራ ህዝብ ጠላቶች የፕሮፖጋንዳ ከበሮ ይመታበታል፡፡
የአማራ ክልል የሚብጠለጠልበትን የብሄረሰቦች መብት የመደፍጠጥ የሃሰት ወሬ ውድቅ የሚያደርገው የቅማንት ጥያቄ ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ ለኦሮሞ፣ለአገው ህዝቦች የተሰጠው የራስን በራስ የማስተዳደር መብትም ሌላው ምስክር ነው፡፡ የአማራ ክልልን በብሄረሰቦች መብት ጨፍላቂነት የሚከሱ ሰዎች የእኛ በሚሉት ክልል በአማራው፣በጋሞው፣በጉራጌው ወላይታው፣ጌዲኦው ላይ  በአደባባይ በማይክራፎን ግልፅ የዘር ማጥፋት አዋጅ የሚታወጅበት ነው፡፡ይህን ጠቅሶ ታገሱ የሚል እውነታውን የሚያሳይ ያልተጋነነ፣ፕሮፖጋንዳ ያልሆነ፣ህዝብን ከህዝብ የማያጋጭ ግን ደግሞ እውነቱን የሚያሳይ የሚዲያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ነገር ካልተሰራ እነዚህን አካላት ከአማራው ህዝብ አናት ላይ ማውረድ አይቻልም፡፡ይህን ለማድረግ ደግሞ የአማራን ክልል የሚመሩት አመራሮች ቀዳሚ መሆን አለባቸው፡፡ በተግባር ሲታይ ግን ይህን በማድረጉ ረገድ አንድ የፌስቡክ ገፅ ያለው ግለሰብ የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረገ ይመስላል፡፡ ይህ የግለሰቦች የማህበራዊ ደረ-ገፅ እንቅስቃሴ ደግሞ ደምፍላት ያለው፣ሙሉ እውነታውን ሊያቀርብም የማይችል፣ጭራሽ ግጭቱን የሚያካርር በመሆኑ ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚበልጥ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ የክልሉ መንግስት ነገ ዛሬ ሳይል የክልሉን ተጨባጭ እውነታ ለኢትዮጵያ ህዝብ በማቅረብ ሃሰትን ቦታ ማስለቀቅ ይጠበቅበታል፡፡
ያደረ አጀንዳን የመግለጥ ስራ
በአሁኑ ወቅት እየተጋጋለ የመጣው አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኝነት ጎራ ከህወሃት ውድቀት ወዲህ የታየው ለውጥ በኦሮሞ ልጆች ትግል የመጣ እንደሆነ ያምናሉ፡፡ስለሆነም ህወሃት ያደርግ እንደነበረው የትግል ጀብዷቸውን እየተረኩ የህወሃት የበላይነትን በኦሮሞ ሊሂቃን የበላይነት ለመተካት ይሻሉ፡፡ ሆኖም የኢትዮጵያ ህዝብ ንቃት ከዚህ አልፎ በመሄዱ ምኞታቸው ስጋ ሊለብስ አልቻለም፡፡ይልቅስ ኦሮሞ ብቻ ታግሎ እንዳመጣው የሚያምኑት ለውጥ የዘረጋው ፖለቲካዊ ዘይቤ እያሳካ ያለው  ነፍጠኛ/አሃዳዊ እያሉ በተለያየ ስም የሚጠሩትን የአማራን ህዝብ ፖለቲካዊ እሳቤ እንደሆነ ያምናሉ፤አምነውም ይብሰለሰላሉ፡፡በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ጎራ እሳቤ መሰረት ኢትዮጵያ የተሰራችበትን እውነት ተቀብሎ፣የሚታረመውን አርሞ፣አንድነቷ ተጠብቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ፖለቲካ የምትሄድበትን መንገድ መተለም የአማራ ብቻ ናፍቆት ነው፡፡ለዚህ ነው ከኦሮሞ  ህዝብ የወጣውን ጠቅላይ ሚንስትር አብይን አፄ ምኒልክን በሚጠሉበት ጥላቻ አምርረው የሚጠሉት፣በአማራ ጉዳይ አስፈፃሚነት የሚከሱት፡፡ይህን ሁሉ ያመጣው አሁን የመጣው ለውጥ የመጣው በኦሮሞ ልጆች ትግል ሆኖ ሳለ የጠቀመው ግን አማራን ነው ብሎ ከማሰብ ነው፡፡
ይህን የተንሸዋረረ እሳቤ ማስተካከል አሁንም በብልፅግና ፓርቲ ውስጥ ያሉ የአማራ መኳንንት ተቀዳሚ ተግባር መሆን አለበት፡፡የማስተካከያ ስራው መጀመር ያለበት ደግሞ የመጣው ለውጥ አክራሪ ብሄርተኞች እንደሚያስቡት ለአማራው የተለየ ያመጣው ነገር እንደሌለ ነው፤ይልቅስ የአማራህዝብ ሃገሩ በለውጥ ምጥ እንዳትሞት ፣ለውጡ እስኪረጋ ድረስ ጊዜ በመስጠት፣ከሁሉ በላይ ኢትዮጵያን በማስቀደሙ ብቻ በይደር ያስቀመጣቸው በርካታ አጀንዳዎች እንዳሉት ማሳወቅ ነው፡፡በይደር የተቀመጡ አጀንዳዎችን ወደማሳቱ ከማለፌ በፊት ግን ሌላ አበይት ነጥብ ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ይኽውም ጠ/ሚ አብይን ወደ ስልጣን ያመጣው ለውጥ ሲረገዝም ሆነ ሲወለድ አማራው በአቶ ደመቀ መኮንን በኩል ከማንም በላይ ለስልጣን ቅርብ ሆኖ ሳለ ለስልጣን ልሙት ሳይል ሃገር የሚያረጋጋው መንገድ ስልጣን መያዙ ስላልመሰለው ስልጣኑ ወደ ኦሮሞ ተወላጁ ዶ/ር አብይ እንዲዞር አድርጓል፡፡ እዚህ ውስጥ ብዙ ትርጉም አለ!
ይህን ትርጉም ለማወቅ የሃገር አጀንዳ ከዘውግ አጀንዳ ዘለግ እንደሚል መረዳትን ይጠይቃል፡፡ ይህን ያደረገ ሰው ናፍቆቱ ገዘፍ ያለው ሃገር የማዳን ተግባር እንጅ የመንደር ልፊያ እንዳልሆነ የሚገባው የሃገርን ትርጉም የሚያውቅ ብቻ ነው፡፡ጠ/ሚ አብይ ከገዛ የዘውጉ ሰዎች ሰባት ጦር የሚወረወርበት ይህ የገባው ሰው ስለሆነ ነው፡፡ጠ/ሚው የሚጠበቅበትን ያህል ሃገር የማረጋጋት ስራ እንዳይሰራ እግር ተወርች የታሰረውም በዚሁ እሳቤ ተሸካሚ የዘውጉም፣የፓርቲውም መካከለኛ እና ዝቅተኛ  ሹመኞች፣የህግ /የፀጥታ አካላት ህቡዕ ስራ ነው፡፡
ስልጣን ላይ ልሙት ሳይል ስልጣን አሳልፎ የሰጠው የአማራው ናፍቆት ሃገር ማዳን ነበር፡፡ የዚህ ስራ ትክክለኛ ትርጉም የሚገባው ግን ለሃገር ግድ የሚለው ብቻ ስለሆነ ክልል እና ሃገር የተሳከረባቸው ሰዎች የሰጡት ትርጉም ሌላ ሆነ፡፡ ስልጣንን አሳልፎ መስጠት ማጉድል መሆኑ ቀርቶ ማትረፍ ተደርጎ ተተረጎመ፡፡በታሪክ ለኢትዮጵያ ሲሞቱ የነበሩ ኦሮሞ አርበኞችን ለአማራ ንጉስ ብለው ነው ወደ ጦርሜዳ ሄደው ቀኝ ገዥን የተፋለሙት ሲሉ የኖሩት የኦሮሞ ብሄርተኞች አሁን የሃገሪቱን የመጨረሻ ስልጣን የያዘው ኦሮሞው አብይ ሲሆንም ኢትዮጵያን የሚለው በስሩ ላሉ አማሮች ተገዝቶ እንደሆነ ሲናገሩ አያፍሩም፡፡ስለዚህ የአማራ መኳንንት በመጣው ለውጥ ሃገር ያሰነበቱ መስሏቸው ሳይከራከሩ ስልጣን አሳልፈው እንደሰጡ፣በዚህም መላው አማራ ከማንም በላይ ደስ እንዳለው ማሳሰብ ሳይስፈልጋቸው አልቀረም፡፡ለዚህ ለውጥ መምጣት የብአዴን ባለስለጣናት ከህወሃት ጋር ያደረጉትን ትንቅንቅ መግለፅ ቢቻልም በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ዘንድ እየበዛ የመጣውን የብቸኛ ጀግንነት አጉል ቀንድ ሊሞርደው ይችላል፡፡
ከዚህ ቀጥሎ የሚመጣው የአማራ ፖለቲከኞችም ሆነ ህዝቡ ኢትዮጵያ ከለውጥ ነውጥ እስክትድን በእናት ሃገራቸው ህመም ላይ ሌላ ራስ ምታት ላለመጨመር ሲሉ ያሳደሯቸው አጀንዳዎች እንዳሉ ማሳወቅ ነው፡፡ይህን ማድረጉ ለውጡ ለአማራ የተለየ ቱርፋ ያመጣ ለሚመስላቸው አካላት እንዲረጋጉ በማድረግ በኩል ጥቅም ይኖረዋል፡፡ከነዚህ አጀንዳዎች አንዱ ወልቃይትን ጨምሮ ሌሎች ከጎንደር ግዛት ላይ በህወሃት ተዘርፈው የተወሰዱ ለም መሬቶች፣እነዚህን ለም መሬቶች ለመወሰድ ሲል ህወሃት በአማራ ህዝብ ላየ የፈፀማቸው ዘር ማጥፋቶች፣ሰው ሰራሽ የዲሞግራፊ ለውጦች፣የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ጉዳይ ነው፡፡ሌላው ቀርቶ ከዚሀ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ከጎንደር ግዛቶች እየታፈኑ ተወስደው ትግራይ እስርቤት ስለታሰሩ እስረኞች ቢነሳ ብዙ ጉድ አለ!
እንደሚታወቀው በደቡብ ክልል ያለው የሲዳማ ዞን ልሂቃን  ወደ ክልል ለማደግ የሚያደርጉትን ትግል አጧጡፈው ያነሱት ህወሃትን ባስወገደው ለውጥ ማግስት ነው፡፡ ይህን ትግል ሲያደርጉ ዛሬውኑ ጥያቄያችን ይመለስ የሚል ፋታ የሌለው ትግል አድርገው፣በርካታ ነዋይ ፈሰስ ተደርጎ ሪፈረንደም አስደርገው ጥያቄያቸው አንድም ሳይሸረፍ መቶ በመቶ መልስ አግኝቷል፡፡ የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄም በአማራ ህዝብ ዘንድ ከዚህ ያነሰ አንገብጋቢነት ያለው ነገር አይደለም፡፡ነገር ግን ከህወሃት ጋር ጠመንጃ እስከመማዘዝ ደርሶ የነበረው የወልቃይትማንነት ኮሚቴ ለውጡን ተከትሎ የመረጋጋት ዝንባሌ አሳይቷል፡፡ ይህ የሆነው የምንወዳት ሃገራችን ባለባት ህመም ላይ ሌላ ህመም ጨምሮ ሞቷን ላለማፋጠን ሲባል እንጅ አማራው በወልቃይት ጉዳይ ላይ የደረሰበት መከራ ቀላል ሆኖ ወይም ለወጡ ጥያቄውን መልሶለት አይደለም፡፡
ሌላው አጀንዳ በአማራው ህዝብ ቁጥር ላይ ያለው ጥያቄ ነው፡፡እንደሚታወቀው ህወሃት አማራውን ለማሳነስ ካለው አምሮት የተነሳ 2.8 ሚሊዮን አማራ የገባበት ጠፋ ሲል በአደባባ ተናግሯል፡፡ይህ የቁጥር መቀነስ ስትራቴጅ አማራው በፓርላማ ያለውን ወንበር ለማሳነስ፣ለክልሉ የሚመደበውን በጀት ለመቁረጥ፣የህዝቡን የፖለቲካ ተደራዳሪነት ግዝፈት ለመቀነስ የተደረገ የህወሃት የዝቅተኝት ስነልቦና የወለደው አካሄድ ነው፡፡ይህ የህዝብ ቁጥር ጉድለት አማራው ሁሉ ይሁን ብሎ የተቀበለው ጉዳይ አይደለም፡፡ ይልቅስ ሃገርን በማስቀደም የተተወ ነገር እንጅ! ሐገርን ባያስቀድም ኖሮ ይህ ሁሉ ህዝብ የገባበት ጠፋ የተባለው የአማራ ህዝብ የህዝብ ቆጠራ ተደርጎ ሎች እንደሚሉት “በቁመናየ ልክ ወንበር ካልተደለደለልኝ ምርጫ ውስጥ አልገባም” በማለት ሃገር የማመሱን ረብሻ መቀላቀል ይችል ነበር፡፡ህዝብ ቆጠራው ቢቀር እንኳን ጠፋ የተባለው ህዝብ ተደምሮ አሁን ባለኝ ህዝብ ቁጥር ላይ ይደመርልኝ ማለት ይቻላል፡፡ግን አልተደረገም፤አልተደረገም ማለት ግን ጥያቄ የለም፤እንደሚታሰበውም ለውጡ ለአማራዊ ፍላጎት የቆመ ስለሆነ አማራው ደስ ብሎት ዝም አለ ማለት አይደለም፡፡ይልቅስ አማራው ኢትዮጵያን የሚለው ከጉድለቱ ጋር ጭምር በመሆኑ ነው፡፡ይህን አስረግጦ ማስረዳት ደግሞ የአማራ መኳንንት ስራ ነው፡፡ ካልሆነ ሃገር ባልሆነ ተረክ ስትታመስ መክረሟ ነው፡፡
እያዚም ቤት እሳት እንዳለ ማሳሰብ
የአማራን ክልል በእጅ አዙር እያመሰ ያለው የቅማንትን ጥያቄ ተገን አድርጎ ከዘውግ ፖለቲከኞች የሚነሳው ተግዳሮት ነው፡፡ የዚህ ተግዳሮት ፊት አውራሪ ህወሃት ስትሆን ቀጣዩ ደግሞ ህወሃት የእስትራቴጅክ አጋሩ እንደሆነ በአደባባይ የመሰከረው የጃዋር ካምፕ ነው፡፡በተለይ ህወሃት የቅማንትን ጉዳይ ያለ ይሉኝታ የገባበት ከመሆኑ ብዛት የቅማንት ኮሚቴ እያለ ለሚጠራቸው ስብስቦች መቀሌ ቢሮ እስከመስጠት ደርሷል፡፡ በዚሁ ኮሚቴ ስም ታጣቂ እያስገባ የአማራ ክልልን የሚያምሰው ነገርም የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ ህወሃት ይህን የሚያደርገው የቅማንት ህዝብ የትግሬ ማንነት አለኝ ባላለበት ሁኔታ ነው፡፡በአንፃሩ የትግራይ ክልል አማራ ነኝ የሚሉ የወልቃይት ህዝቦች እና ወደ አማራ ክልል መካለል እንፈልጋለን የሚሉ የራያ ህዝቦች  ያሉበትን መሬት በጉልበት ዘርፎ ወስዶ፣ሰዎቹን መብታቸውን ረግቶ በግዞት እያኖረ ነው፡፡
ይህን ህወሃት መራሹ የትግራይ ክልል አስተዳደር የሚያደርገውን ግፍ ለመታገል የወጡ የወልቃይት ማንነት እና የራያ ማንነት ኮሚቴዎች ግን ወደ ግዛቱ እንካለል ከሚሉለት የአማራ ክልል አስተዳደር ይህ ነው የሚባል እርዳታ አግኝተው አያውቁም፡፡የትግራይ ክልል አስተዳደር ምንም በማይመለከተው የቅማንት ማንነት ኮሚቴ ውስጥ ይህን ያህል የወሳኝነት ሚና ሲወስድ የአማራ ክልል አማራ ነኝ ለሚሉ ግን ደግሞ በህወሃት ከባድ ቀንበር ስር ላሉ ህዝቦች ይህ ነው የሚባል እርዳታ ያለማድረጉ የመፋዘዙ እንጅ የብልህነቱ ምልክት ሆኖ አይታየኝም፡፡በርግጥ ህወሃት በአማራ ክልል ላይ እንደሚያደርገው የአማራ ክልል ሹማምንትም ወደ ትግራይ ክልል ታጣቂ እያሰረጉ ማተራመስ ልክ መንገድ አይደለም፡፡ከዚህ በመለስ ግን አማራ ነን በማለታቸው አበሳ ለሚያዩ ህዝቦች ድጋፍ ማሳየት ተገቢ ነገር ነው፡፡ይህ ዋናው ነገር ሆኖ እግረ መንገዱን ለህወሃትም እዚያም ቤት እሳት አለ የሚል መልዕክት መስጠቱ አይቀርም፡፡ ይህ ደግሞ የትግራይ ክልል አስተዳደር የራሱ መታወቂያ የሆነውን የህዝቦች መብት መደፍጠጥ ወደ አማራ ክልል የማላከክ ፕሮፖጋንዳውንም ሆነ ወደ አማራ ክልል የሚልከውን ፈተና ለመቀነስ ይረዳል፡፡