Monday, September 18, 2017

ፋሽስት ሆይ! ጠገዴ አንድ ቤተሰብ፣ ድንበሩም ተከዜ ነው! (ልሳነ ግፉዓንና የጠለምት አማራ ማንነት ጥምረት ኮሚቴ)


Welkait Tsegede

ፋሽስቱ የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጭ ግንባርና ተላላኪው ብአዴን በአዲሱ አመት ዋዜማ ለመላው የጎንደር ህዝብ የሰጡት ስጦታ ቢኖር ሰላምና አንድነትን ሳይሆን አካሉ የሆነውን የጠገዴን ማህበረሰብ ለሁለት እንደ ቅርጫ መቀራምትን ነው።
ታላቋን ኢትዮጵያ የማፍረስና ህዝቧን የማተራመስ ተልዕኮ እንደ ቀደምት ባንዳ አባቶቹ ከጠላቶቻችን የተሰጠው የትግራዩ ወራሪ ቡድን የአማራን ህዝብና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተቀዳሚ ኢላማው አድርጎ በውድ ሃገራችንና በኩሩው ህዝባችን ላይ መርዙን መዝራት ከጀመረ እነሆ 26 የፅልመት አመታት ተቆጠሩ።
ከሽፍትነት ዘመኑ ጀምሮ ታሪካዊና ለም የሆኑትን የጎንደር መሬቶች በተቀዳሚነት ኢላማው ያደረገው ወራሪው ተ.ሃ.ት የተከዜን ወንዝ በመሻገር የወልቃይትን መሬት ከረገጠበት ከ1972 ዓ.ም ጀምሮ በወገናችን ላይ ያደርስ የነበረው ዝርፊያ፣ እስራት፣ ድብደባና፣ ግድያ እስከ ዛሬም ድረስ የቀጠለ ሲሆን በተለይም ከአንድ አመት በፊት የወልቃይትን ህዝብ ሙሉ ውክልና ይዘውና የህዝብን ጥያቄ አነግበው በሰላማዊ መንገድ ፍትህን የጠየቁ የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴ መሪዎችና አባላት በሽብርተኝነት ተወንጅለው በዋና ዋና የህወሃት የማሰቃያ ካምፖች ውስጥ መከራን እየተቀበሉ የሚገኙ ሲሆን፤ወረራውንና መስፋፋቱን በፍፁም ጭካኔና ማንአለብኝነት የቀጠለው ይህ እኩይ ቡድን ወደ ጠገዴና ጠለምት ያደረገውን ወረራ የተቃወሙትን ታሪክ ነጋሪ የሃገር ሽማግሌዎችን፣ ትውልድና ሃገር ጠባቂ ጎልማሳዎችን፣ እንዲሁም ሃገርና ታሪክ ተረካቢ የሆነውን ወጣት ትውልድ በግልፅና በስውር በመጨፍጨፍ ካጠፋ በኋላ ዕርስታችንን በሃይል ወደ ትግራይ በመጠቅለል በይፋ የምትገነጠለው ትግራይ አካል ከተደረገ እነሆ ሃያ ስድስት የሰቆቃ አመታት አሳለፍን።
ምንም እንኳ ህዝባችን በፋሽስቱ ህወሃት የጭቆና አገዛዝ ስር ሆኖ ቃላት ሊገልፁት በማይቻላቸው መከራና ስቃይ ውስጥ ቢገኝም ጭቆናንና ባርነትን አሜን ብሎ መቀበል ከአባቶቹ አልወረሰምና በሚቻለውና ባገኘው ቀዳዳ ሁሉ ተጠቅሞ የጠላቱን እኩይ ሴራ በማክሸፍ ላይ ይገኛል። ይሁንና ይህ ህዝባዊ ተጋድሎ እረፍት የነሳውና ኢትዮጵያን የማፈራረስና ትግራይን የመገንጠል ሰይጣናዊ ተልዕኮ እያኮላሸበት የሚገኘውን የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ህዝብ ለማዳከምና ከፋፍሎ ለማጥቃት በማለም አንድን ቤተሰብ የሆነውን የጠገዴ ማህበረሰብ ለሁለት በመክፈል ግማሹን ጠገዴ ሌላኛውን ግማሽ ፀገዴ በማለት ለያይተው የሚቻላቸውን ክፉ ተግባር ሁሉ ሲፈፅሙብን ኖረዋል።
ይሁን እንጂ ምንግዜም ቢሆን ጀግና መውለድ የማታቆመው የጎንደር እናት ዛሬም እንደ ትላንቱ አንድ ጠገዴ!!! ብለው በተነሱ ልጆቿ አማካኝነት ህዝባዊ ትግሉን በማፋፋም የፋሽስቱን ጎራ እያንቀጠቀጡት ይገኛሉ። “ወላድ በድባብ ትሂድ” እንዲሉ በጠገዴ የቁርጥ ቀን ልጆች የማያወላዳ ጥያቄ የተሸበረውና የዘመናት ሴራው በዜሮ የተባዛበት የተገንጣዩ ጎራ ከጳጉሜ 1, 2009 ዓ.ም ጀምሮ አንዳች የአማራ ህዝብ ድጋፍ በሌለውና እርሱ ህወሃት በአምሳሉ ጠፍጥፎ ከሰራው ብአዴን ተብዬ የአሻንጉሊቶች ስብስብ ጋር በመሆን አንዱን የጠገዴ ቤተሰብና ዕርስቱን ለሁለት በመከፈል መቀራመታቸውን በየፊናቸው እያወጁ ይገኛሉ።
የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ህዝብ ጥያቄ ግልፅና አንድ ነው። ይሃውም ህዝቡ ጎንደሬ/አማራ፣ መሬቱ የጎንደር፣ ድንበራችን ተከዜ ነው! የሚል ነው። ከዚህ ታሪክና ማንነትን መሰረት ካደረገ ህዝባዊ ጥያቄ አንዳች ጎደሎና እንከን የታከለበት ሽርፍራፊ ምላሽ ህዝባችን እንደማይቀበል የአለፉትን ሃያ ስድስት የፅልመትና የጭቆና ዘመናትን በፅናት በማለፍ ዛሬ እንደ አዲስ አይነቱንም ሆነ ይዘቱን ቅንጣት ሳይቀር ዳግም በወጣቱ ትውልድ መነሳቱ አብይ ማረጋገጫ ነው።
ታዲያ ይህን ታሪካዊ እውነታ አንዴ “በወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ አቅራቢ” ኮሚቴ አማካኝነት፣ ሌላ ጊዜ “ጠገዴ አንድ ነው” በሚለው የጠገዴ ህዝብ ጥያቄ ሳይወድ በግዱ እንዲጋፈጠው የተደረገው ፍሽስቱና ተስፋፊው የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጭ ግንባር “የማይተማመን ጓደኛ በየወንዙ ይማማላል” እንዲሉ ለሃያ ስድስት አመታት በሃይል ከልሎ ሲበዘብዛቸው የኖሩትን የጠገዴ ወገኖችን በተለይም ዕርስታችን የሆኑትን የግጨውና የጎቤ ጎንደሬ/አማራ መንደሮችን ትግሬ ያደረገ የትግራይን ድንበር ከአማራ ጋር ተካልያለሁ በማለት ሎሌዎቹን ሰብስቦ ከበሮ እየደለቀና ሻምፓኝ እየተራጨ ይገኛል።
እኛ በመላው ዓለም የምንገኝ የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ተወላጆች ዛሬም እንደትላንቱ በአንድነት ከህዝባችን ጐን በፅናት በመቆም የትግል አጋርነታችንና አንድነታችን እየገለፅን ከጳጉሜ 1, 2009 ዓ.ም ጀምሮ በህወሃትና በብአዴን መሪዎች አማካኝነት የታወጀው ጠገዴን ከሁለት በመክፈል በተለይም የጎንደር/አማራ ለምና ታሪካዊ የሆኑትን የግጨውና የጎቤ መንደሮችን ወደ ትግራይ መከለል ፍጹም ሰብአዊነት የጎደለውና አንድን ቤተሰብ ለሁለት የሚከፍልና የሚለያይ ጭራቃዊ ተግባር በመሆኑ የምንፀየፈው አጥብቀን የምናወግዘው መሆኑን እየገለፅን፤ ትላንት ከቀጣሪዎቹ በተሰጠው ኢትዮጵያን የማፈራረስ ባንዳዊ ተልዕኮ አንዱ የሆነውን ኤርትራን የማስገንጠልና የህጋዊና ዓለም አቀፋዊ ድንበር ባለቤት የማድረግ ሴራና ድራማ በቅጡ መከወን ያልተቻለው ፍሽስቱ ሟች መለስ ዜናዊ  ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ሊያስፈፅም አልጀርስ ላይ ከኤርትራ ጋር የተስማማበትንና በአንፃሩ ደግሞ የኢትዮጵያን ህዝብ ከጅምሩ አጥብቆ የተቃወመውን መሰሪ ውል ሲያፈርስ እንደ ዋነኛ ምክንያት ሲቀላምድ የነበረው “አንድ ቤተሰብ ለሁለት የሚከፍል” ፍርድና የድንበር ማካለል አልቀበልም በማለት ነበር።
ዛሬ የሙት መሪያቸው ራዕይ ወራሾች ነን በሚል በየመድረኩ ሲምሉና ህዝብን ሲያደነቁሩ የሚውሉ ውልደ ፋሽስቶች ህዝባችን በወኪሎቹ አማካኝነት “እኛ አንድ ቤተሰብ ነን!” “ጠገዴ አንድ ነው!” በሚል ያቀረበው ህዝባዊ ጥያቄ ለአልጀርሱ በተባው የክህደት ምላስና ህሊናቸው “አንድ ቤተሰብ ለሁለት የሚከፍል” ፍርድና የድንበር ማካለል አንቀበልም ማለትን እረስተው ህዝባችንን ዛሬም ድረስ ዘመን መለወጫን እየጠበቁ ያስለቅሱታል። ዕርስታችንም ታላቋን ትግራይ ለመመሥረት በሚል ቅዥት ወደ ትግራይ በማካለል ለሕዝባቸው የአዲስ ዓመት ስጦታነት ያውሉታል።
ይሁን እንጂ ዛሬም ህዝባችን በፍፁም ጨዋነት ያቀረበው ሰላማዊና ህጋዊ ጥያቄ ፍትሃዊ ምላሽ ሳይሰጠው በመቅረት በተገንጣዮች የእብሪት እርምጃ አሁንም እንዲለያይ በግፍ የተፈረደበት ቤተሰባችን ዳግም አንድ ሆኖ በሃገሩ ላይ በነፃነትና በእኩልነት መኖር እስኪችልና ሰላሙና አንድነቱ እስኪረጋገጥ ድረስ ትግላችን ከምንግዜውም በላይ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ለፍሽስቱ ህወሃትና ለተንበርካኪው ብአዴን አመራሮች፣ አባላትና፣ ደጋፊዎች እያሳወቅን፤ በዚህም ምክንያት ለሚደርሱት ማንኛቸውም ሃገራዊና አካባቢያዊ ችግር ብቸኛ ተጠያቂው ፋሽስቱ የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጭ ግንባርና ተላላኪው የብአዴን አመራር አካላት መሆናቸውን ከጥብቅ ማሳሰቢያ ጋር እንገልፃለን።
ጠገዴ አንድ ቤተሰብ፣ ድንበሩም ተከዜ ነው!
ልሳነ ግፉዓንና የጠለምት አማራ ማንነት ጥምረት ኮሚቴ
መስከረም 1, 2010 ዓ.ም
ሰሜን አሜሪካ

ኦሮሚያና በሶማሌ ክልሎች መካከል የተከሰተውን ግጭት የሚያብራሩ አምስት ነጥቦች

by maleda times



BBC AMHARICካርታ

አሁኑ ወቅት በኦሮሚያ እና በሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች በተቀሰቀሱ ግጭቶች በምክንያት የሰዎች ህይወት ጠፍቷል፤ ከሃምሳ አምስት ሺ በላይ የሚቆጠሩ ዜጎችም ከመኖሪያቸው እንዲፈናቀሉ ተገደዋል።
የኦሮሚያ ክልል መንግሥት፤ የሶማሌ ልዩ ፖሊስን እንዲሁም ሚሊሻዎች ወደ ኦሮሚያ ዘልቀው በመግባት ጥቃት አድርሰዋል ሲል የሚከስ ሲሆን፤ የሶማሌ ክልል በበኩሉ አጥቂዎቹን በኦሮሚያ ክልል የሚደገፉ ናቸው ሲል በኮሚኒኬሽን ቢሮው በኩል አሳውቋል። መወነጃጀሉና የቃላት ምልልሱ መካረር የክልሎቹ መንግስታት ግንኙነት ያለበትን ደረጃ ከማሳበቁም ባለፈ የግጭቶቹን መረር ማለትም አመላካች ነው። ይሁንና በሁለቱ ክልሎች መካከል ውዝግብ፣ ግጭት፣ ሲያልፍም ደም መፋሰስ ሲያጋጥም የአሁኑ የመጀመሪያው አይደለም።
1.አጨቃጫቂ ወሰን
በቆዳ ስፋቱ ከአገሪቱ ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘው የኦሮሚያ ክልል፤ ከሁለተኛው ሰፊ የሶማሌ ክልል ጋር የሚያዋስነው 1410 ኪሜ ድንበር አለው። ይህ ድንበር ግን ክልሎቹ አሁን ያሉበትን ቅርጽ ይዘው ከተመሰረቱበት ጊዜ አንስቶ ውዝግብ አያጣውም። ውዝግቡን ፈትቶ ወሰኖቹን መልክ ለማስያዝ ታስቦም ሕዝበ ውሳኔ ከ400 በሚበልጡ ቀበሌዎች በጥቅምት ወር 1997 ዓ.ም ተደርጓል።
በሕዝበ ውሳኔው መሰረት ከ80 በመቶ በላይ የሚሆኑ ቀበሌዎች በኦሮሚያ አስተዳደር ሥር እንዲጠቃለሉ የተወሰነ ቢሆንም የወሰን ማካለል ሥራው ተግባራዊ ሳይሆን ቆይቷል። ይህም በየጊዜው ለሚነሱ ግጭቶች አባባሽ ምክንያት መሆኑ አልቀረም።
ባለፈው ሚያዝያ ግን የሁለቱም ክልሎች ፕሬዚዳንቶች ሕዝበ ውሳኔውን ተግባራዊ ለማድረግ ያስችላል የተባለ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱ በተፈረመበት ወቅት የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ለማ መገርሳ "ትልቅ ድል" መገኘቱን ሲገልፁ፥ የሶማሌ ክልል አቻቸው አብዲ መሃመድ በበኩላቸው "በሁለቱ ወንድማማች ሕዝቦች መካከል ዳግመኛ ግጭት አይኖርም።'' ብለው ነበረ።
የኦሮሚያ ክልል ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋም የችግሩ ምንጭ ''የድንበር ጉዳይ እንዳልሆነ የሚያረጋግጥልን፤ ድንበር በማንጋራባቸው አካባቢዎች ጭምር ጥቃት ሲፈፀም የነበረው። የድንበሩን ጉዳይ በ1997 ሕዝበ-ውሳኔ መሰረት ለመፍታት በተደረሰው ስምምነት መሰረት እየሰራን ነው።ሥራውም ሰባ በመቶ በላይ ተጠናቋል።'' ሲሉ ሌላ ምክንያት ሊኖር እንደሚችል ይጠቁማሉ።
2.የተፈጥሮ ብት ፉክክር
በኢትዮጵያና ኬንያ ድንበር የሚገኙ የኦሮሞ እና የሶማሌ ክልል አርብቶ አደርና ከፊል አርብቶ አድር ሕዝቦችን ግንኙነት ያጠኑት የማኅበረሰባዊ ሥነ-ሰብ ተመራማሪው ፈቃዱ አዱኛ እንደሚሉት ፉክክርና ግጭት በተለይ የቦረና ኦሮሞዎችና የአካባቢው ሶማሌ ጎሳዎች መገለጫዎች ሆነው ቆይተዋል ይላሉ።
ፉክክርና ግጭቶቹ በብዛት ውሃ እና የግጦሽ መሬትን በመሳሰሉ የተፈጥሮ ሃብቶች ተጠቃሚነት ዙርያ የሚያጠነጥኑ ቢሆንም ከቅርብ ጊዜ አንስቶ የብሔር መልክ እየያዙ መምጣታቸው ይወሳል።
በአገሪቱ ፖለቲካዊ አወቃቀር የብሄር ድንበሮች የፖለቲካ ድንበሮች ጭምርም በመሆናቸው፤ በማኅበረሰቦቹ ዘንድ ያለውን የፉክክር መንፈስ ክልላዊ ገፅታ አላብሶታል ሲሉ ይከራከራሉ አቶ ፈቃዱ። ለዚህም በማሳያነት የሚጠቅሱት ከዚህ ቀደም በአንፃራዊነት ሰላማዊ ግንኙነት የነበራቸው የአርሲ ኦሮሞና አጎራባች የሶማሌ ጎሳዎች ደም ወዳፋሰሰ ግጭት መግባታቸውን ነው።
አካባቢዎቹ ለድርቅ ተጋላጭነታቸው ከፍ ያለ መሆኑ በተፈጥሮ ሃብት ፍላጎቶች ላይ ለሚነሱ ቅራኔዎች ተጨማሪ ነዳጅ የሆኑ ይመስላል።



ተፈናቃዮችን የሚያሳይ ምስል

3.የሕዝበ-ውሳኔ ራስ ምታት
ለተመራማሪው ፈቃዱ አዱኛ፤ መንግሥት ለአካባቢዎቹ ወሰን ተኮር ግጭቶች ፖለቲካዊ መፍትሄ ለመስጠት ባደረገው እንቅስቃሴ ሕዝበ-ውሳኔ ማከናወኑ የአካባቢዎቹን ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ ነው። የአካባቢው ኗሪዎች በአብዛኛው አርብቶ አደሮች እንደመሆናቸው ከሥፍራ ሥፍራ ይንቀሳቀሳሉ። ይህም ወሰኑን ቁርጥ ባለ ሁኔታ ማስቀመጥን አዳጋች ያደርገዋል።
የህዝበ-ውሳኔው ውጤት በሁለቱ ክልሎች መካከል የተነሳውን ጥያቄ ምላሽ ሰጥቷል ቢባልም የተካሄደበትን ወቅት መሰረት ያደረገ ሌላ ጉዳይ አሁን እንደተነሳ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር "ከሶማሌ ክልል በኩል የሚነሳው ጥያቄ ሕዝበ-ውሳኔው የተካሄደበት ወቅት የሶማሌ ክልል የራሱን ግዛት ሊያስጠብቅ በማይችልበት አቅም ላይ በነበረበት ጊዜ በመሆኑ ብዙ ግዛት ተወስዶብኛል የሚሉ ጥያቄዎች እያነሳ ነው።" ይላሉ።
4.ሞትና መፈናቀል
ባለፈው ነሐሴ የተካረሩ ግጭቶችን ያስተናገደው የሚኤሶ አካባቢ ለወትሮውም ለዚህ መሰል ፍጭቶች ባይታወር አይደለም። ሕዝበ ውሳኔን ባስተናገደው የ1997 ዓ.ም በመኢሶና በቦርደዴ አካባቢዎች በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን እንዲፈናቀሉ ያስገደዱ ግጭቶች ተከስተዋል ይላል የአይ ዲ ፒ ፕሮጄክት ሪፖርት።
በ2005 ዓ.ም ደግሞ በሞያሌ አካባቢ በተቀሰቀሰ የሁለቱ ብሔር አባላት ግጭት ከ20ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች ሸሽተው ኬንያ መግባታቸውን የኬንያ ቀይ መስቀል ማህበር በዚሁ ወቅት አስታውቆ ነበር። በወቅቱ ለግጭቱ መቀስቀስ ምክንያት ተደርጎ የተጠቀሰው በግጦሽ መሬት ይገባኛል ቢሆንም ግጭቶቹ ብሄር ተኮር ይዘት እንዳላቸውም አብሮ ተዘግቧል።
ባለፈው ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባደረጉት ንግግር የሚከሰቱት ግጭቶች መንስዔ የብሄር ይዘት አለው ባይሉም፤ በግጦሽ መሬትና በውሃ የተቀሰቀሰ ነውም አላሉም። ከዚያ ይልቅ ለጉዳዩ ቅርበት አላቸው ያሏቸውን የአካባቢውን አስተዳዳሪዎችን ወቅሰዋል።
5.ማኅበረ-ባህላዊ ልዩነቶችና አንድነቶች
የኦሮሞና ሶማሌ ሕዝቦች ከምስራቅ ኩሽ የቋንቋ የዘር ግንድ የሚመዘዙ ሲሆን በኢትዮጵያ ሶማሌዎችና በተለይም እስልምና በገነነባቸው የኦሮሞ አካባቢዎች መካከል መልካም የሚባል ግንኙነት ተመስርቶ መቆየቱን የሚያነሱት አቶ ፈቃዱ፤ ባሌ ውስጥ የሚገኘው የሼክ ሁሴን መስጊድ በሁለቱም ሕዝቦች እንደ ቅዱስ ቦታ መቆጠሩን ያስታውሳሉ።
የሶማሌና የኦሮሞ ሕዝብ አብሮ ከመኖሩ አንፃር በርካታ አንድ የሚያደርጓቸው ነገሮች እንደሉ የሚጠቅሱት የፖለቲካል ሳይንስ መምህሩ፤ ምንም እንኳን እነዚህ ግዛቶች በወሰን ቢከፋፈሉም አሁንም የሁለቱ ህዝቦች የሚንቀሳቀሱባቸው ከተሞች አሉ፤ በማለት የሁለቱ ሕዝቦች አብሮነት እንደማይቋረጥ ይናገራሉ።