Monday, January 14, 2013

አበበ ጉዑሽን በላ

           

ጃንዋሪ 12፡2013 በያሬድ አይቼህ
“በአለም ማየት የምትፈልገውን ለውጥ ሆነህተገኝ።”
ማህተማጋንዲ
ኢሳት ጃንዋሪ 8፡2013 ላይ እንዲህ የሚል አጭር የቪዲዮ ሰበር ዜና ለጥፎ ነበር፡ “የ FBI መርማሪዎች አበበ ገላውን ለመግደል የታቀደ ሴራ አከሸፉ(።) በሴራው የተሳተፉ የህወሃት ሰላዮች ምርመራ እየተደረገባቸው
ነው።” ‘ሴረኛ’ ከተባሉት ሰዎች አንዱ አቶ ጉዑሽ አበራ ነው።
ትናንት አርብ ምሽት አቶ ጉዑሽ አበራ ነው የተባለ ሰው በፓልቷክ የሲቪሊቲ ክፍል ተጋብዞ በተደረገለት ቃለ ምልልስ ስለ ጉዳዩ የሰጠውን ማብራሪያም ሰማሁ። ምንም እንኳን የኤፍ.ቢ.አይ ምርመራ አልተቋጨም የሚል
ድምዳሜ በተደጋጋሚ ቢሰማም ፡ እኔ ግን የራሴ ድምዳሜ ላይ ደርሻለሁ።
ጉዳዩን እንዲህ ነው ማየው፦ ጉዑሽ የአቶ መለስ ዜናዊ ደጋፊ ነው። አቶ መለስ መሞታቸውን አስመልክቶ ከሰዎች ጋር በፉስቡክ እሰጥ-አገባ ይያያዝና ሰዎች አንጀቱን ያሳርሩታል። እሱ ደግሞ በንዴት ‘የጻፈውን’ ይጽፋል።
ይሄ ነው ጉዳዩ። ከዚህ በላይ ሌላ ነገር አላየሁበትም። ተሳስቼ ይሆናል ፤ ግን ይሄው ነው።
እኔን ግን ያሳሰበኝ የጉዑሽ ‘ጽሁፍ’ ሳይሆን የዲያስፓራ ተቃዋሚዎች ምን ነክቶን ነው እንደዚህ የጦዝነው? እንዴ! ለመሆኑ ኢህአዴግ ፍርደ-ገምድል ፡ አምባገነንና ፋሺስት ነው እያልን እኛም ያው ነን እንዴ? የአሜሪካንን የፍትህ ስርዓት ተጠቅመን ሰዎችን ለማሸበር መሞከራችን በእውነት በጣም አሳፋሪ ነው። ይህን ስል ጋዜጠኛ አበበ ገላው የሞት ዛቻን በቀላሉ ይመልከት ማለቴ አይደለም ፡ ግን የሌሎቻችን ጉዳዩን ማጋጋል አልገባኝም
ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙን “ለምን ፎቶ ግራፍ አነሳሽ?” ብሎ 14 ዓመት የፈረደባትን የኢህአዴግን ፋሺስታዊ የፍርድ ስርዓት እየተቃወምን ፡ እኛ ያው ሆነን መገኘታችን ምን ያህል የአላማ እና የስነ-ምግባር ክስረት ውስጥ ያለን ህብረተሰብ
መሆናችንን ነው ለኔ ሚጠቁመኝ።
ርዕዮት አለሙ ያነሳችው ፎቶግራፍ ይሆናል የተባለውን አይታችሁታል? እኔ አይቼዋለሁ። ፎቶግራፉ ላይ ሚታየው ፡ በእኔ ግምት ፡ አንድ ጎረምሳ የእናቱን ወይም የእህቱን ቀይ ጥፍር ቀለም ሰርቆ የጻፈው “በቃ” የሚል ጽሁፍ ነው። ለዛ ነው ርዕዮትን ለ14 ዓመት የኢህአዴግ ፋሽስታዊ ፍርድ ቤት የፈረደባት።
ልብ በሉ፦ ጉዑሽ አበራ ከፌስቡክ ጽሁፍ ፡ ርዕዮት አለሙ ከፎቶግራፍ ጽሁፍ የተነሳ ነው አሁን ያሉበት ችግር ውስጥ የወደቁት። የፓለቲካ ውጥረታችን መርገብ የሚችለው “አይንን ያፈሰሰን አይኑን ማፍሰስ” በሚል ፋራ አስተሳሰብ
አይደለም ፡ አልሆነምም ፡ ሊሆንም አይችልም። ታላቁ የሰለማዊ ትግል ጀግና ማህተማ ጋንዲ ፡ “በአለም ማየት የምትፈልገውን ለውጥ ሆነህ ተገኝ”* ያሉት እጅግ ትልቅ ጥበብ ነው።
የዲያስፓራም ተቃዋሚዎች በኢትዮጵያ ማየት የምንፈልገውን ለውጥ እኛ በተግባር ካላሳየን ፡ እኛም ሌላ አምባገነኖች ነው የሆነው። የህግን ሽፋን ተጠቅመን ሌሎችን የምናንገላታ ፡ የምናሰቃይ እና የምናሸብር ከሆንን ፡ እኛና ኢህአዴግን ምን ለየን? … መልሱልኝ እንጂ? … ምን ለየን?!
*”Be the change that you wish to see in the world.” Gandhi
staff reporter | January 13, 2013 at 12:21 pm | Categories: AMHARIC NEWS | URL: http://wp.me/p2gxmh-1kg
Comment  

         

No comments:

Post a Comment