Wednesday, January 16, 2013

ጥያቄዎቻችን በጆሮ ዳባ ልበስ ሊታለፉ አይገባም፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ገዢው ፓርቲ ተገደው እንዲሰሙ የማድረግ ህዝባዊ ትግል ይቀጥላል!! ከ33ቱ የፔቲሽን ፈራሚ ፓርቲዎች ባቀረብነው ጥያቄ ዙሪያ በቀጣይ የጋራ አቋም ላይ የተሰጠ መግለጫ




Gudu  Kassa
ከ33ቱ የፔቲሽን ፈራሚ ፓርቲዎች ባቀረብነው ጥያቄ ዙሪያ በቀጣይ የጋራ አቋም ላይ የተሰጠ መግለጫ
  1. 1. መግቢያ
በአዳማ ከተማ በ2005 ምርጫ የጊዜ ሠሌዳ ላይ ለማወያየት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰበሰበን ወቅት ከተሣታፊ 66 ፓርቲዎች 41ዱ ከጊዜ ሠሌዳው በፊት የውድድር ሜዳውን መስተካከል በሚመለከቱ አበይት የምርጫ ጉዳዮች ልንወያይ ይገባል ከሚለው ኃሣብ በመነሣት እና በጉዳዩ ለመግፋት ፔቲሽን ፈረምን፡፡ በመቀጠልም በ29/02/05 ዓ.ም 18 ጥያቄዎችን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ /ኢብምቦ/፣ 13 ጥያቄዎችን ደግሞ በ08/04/05 ለክቡር ጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት፣ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አፈጉባኤ ጽ/ቤት አቅርበን ከቦርዱ ጥያቄአችሁ “ውሃ አያነሳም” በሚል ሙሉ በሙሉ ውድቅ መደረጉ በ10/04/05 ዓ.ም በቃል ሲገለጽልን፤ ከጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት፣ ከህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አፈጉባኤ ጽ/ቤት መልስ እየጠበቅን መሆኑን ገልጸን መልስ መጠባበቃችንን ቀጠልን፡፡
ነገር ግን ጥያቄዎቻችን ግልጽና የማያሻሙ ቢሆኑም ምርጫ ቦርድ “ጆሮ ዳባ ልበስ” በሚል ለጥያቄአችን መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ አፀደቅሁ ባለው የጊዜ ሠሌዳ መሠረት በገዢ ፓርቲ አይዞህ ባይነት ወደ ምርጫው አፈፃፀም ገብቷል፡፡
  1. 2. በሂደቱ የተገኙ የውሳኔ መነሻ ነጥቦች፤
2.1 ምርጫ ቦርድ ምላሽ የሰጠን የቦርዱ ሰብሳቢ በአዳማ ስብሰባ ላይ፣ የቦርዱ ጽ/ቤት ኃላፊ ደግሞ በ06/03/05 በአዲስ አበባ ቢሮአቸው፣ የጥያቄችንን አግባብነት አምነው የውይይት /ምክክር መድረክ ይዘጋጃል በማለት የሰጡትን መልስ በማጠፍ/ ቃላቸውን በመካድ መሆኑ፤
2.2 ከቦርዱ ምላሽና አካሄድ በመነሣት እኛም የቦርዱን “. . .የገዢው ፓርቲ ወገንተኝነትና ጉዳይ ፈፃሚነት . . .”፣ ምርጫውን ለማስኬድ እየገፋ ያለው “. . .ለኢህአዴ ብቻ በተመቻቸ ሜዳ . . .” መሆኑን፣ የሚሉ አቋሞቻችንን በገለጽንበት ሂደቱ ወደ ተግባር የተሸጋገረ መሆኑ፤
2.3 የቦርዱ ሰብሳቢ በ24/04/05 በኢቲቪ ቀርበው ጥያቄአችንን በማጣጣል . . .” ከ33ቱ ፈራሚዎች 5ቱ የምርጫ ውድድር ምልክት ወስደዋል. . .”፣ “. . . በርካቶች እየመጡ ጥያቄው እኛን አይመለከተንም እያሉን ነው . . .” ከማለት አልፈው “. . .የኮሚቴው አባለት ህጋዊ ውክልና ባይኖራቸውም በሆደ ሰፊነት አነጋግረናቸው ተማምነን ተለያይተናል . . .” ሲሉ ፍፁም የክህደትና የመከፋፈል ሴራ የተሞላ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ እንደ ሰብሳቢው መግለጫ 5ቱም ምልከት ቢወሰዱ እንኳ የ28ቱ ጥያቄ ውድቅ መደረግ ያለበት በጥያቄዎች ይዘት /ፋይዳ ወይስ በጠያቂዎች ቁጥር? በብዛትስ ቢሆን 28 ፓርቲዎች ጥያቄውን ለማቅረብ ትንሽ ቁጥር ነውን? የሚሉትን ጥያቄዎች አኑረን ይህ ምን ያመለክታል ወደሚለው ስንገባ፤
ሀ. ቦርዱ በጋራ ባቀረብናቸው ጥያቄዎች ጭንቅ ውስጥ መግባቱን ሲሆን ለዚህም ምላሹን በጽሁፍ ለመስጠት እንኳ ፈቃደኛ ያለመሆኑ ማሣያ ሲሆን፣ እንዲሁም በትብራችን የተደናገጠውን አይዞህ ባዩን ኢህአዴግ ለመከላከል እየተወራጨ መሆኑን ደግሞ የእነ ወ/ሮ የሺ፣ የአቶ ነጋ እና የፕ/ር መርጋ መግለጫዎች /ምላሾች በግልጽ የሚያሳይ መሆኑን፤
ለ. ለእኛ የአካባቢ ምርጫ በህዝቡ ውስጥ መሠረት ለመጣል ዘልቆ መድረሻ በመሆኑ ትኩረት ሰጥተን እየተንቀሳቀስን መሆናችንን በተደጋጋሚ ብንገልፅም፤ ከተሰጠን ምላሽ የምንረዳው ገዢው ፓርቲ /መንግሥት ጥያቄአችንን ከጥቅም ጋር በማገናኘት የተለየ ትርጉም በመስጠት ለማሳነስ እየጣረ መሆኑን፤
ሐ. እስካሁን ድረስ እንኳን ፔቲሽን ፈራሚዎች 5ቱ፤ ከኢህአዴግና አጋር ፓርቲዎች በቀር ጥያቄአችንን በይፋ /በአደባባይ የተቃውመ ወይም አይመለከተንም ያለ አለመኖሩ፣ ይልቁንም ሁሉም ማለት በሚቻልብት ሁኔታ ለጥያቄው በይፋ ድጋፍ የገለፁበት የጥያቄአችንን ትክለኛነትና ፖለቲካዊ አንደምታ በግልጽ የሚያሳይ መሆኑን፤
መ. ምርጫ ቦርድ በህግ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ነፃ፣ ፍትሀዊ፣ ተአማኒና አሳታፊ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ለማስፈጸም ገለልተኛ ያለመሆኑን፤ ነፃነቱ ፣ ፍላጎትም ሆነ ተነሣሽነት የሌለው መሆኑን፤
ሠ. በህዝብ ውስጥ ጠንካራ የለውጥ ፍላጎትና ይህንንም በምርጫ ለማምጣት ከፍተኛ ተነሳሽነት ቢታይም መራጩ ዜጋ በሚጭበረበር ወይም ድምፁ በሚነጠቅበት ምርጫ የተሰላቸ /ተሥፋ የቆረጠ/ ቢመስልም ከጉዳዩ አሳሳቢነትና ካለው አገራዊ ፋይዳ አኳያ ጥያቄአችንን በትኩረትና በንቃት እየተከታተለ መሆኑን፤
ረ. በጥያቄአችን የተነሱት ጉዳዮች በምርጫ ባለድርሻ አካላት በአጠቃላ እንዲታወቁ እየተደረገ መሆኑን እንዲሁም የሁሉንም ትኩረት በመሳብ የመወያያ ርዕስ መሆናቸውን፤ ወዘተ
በአጠቃላይ ከስብስቡ የጋራ ጥያቄ አቀራረብ የተገኘው ትምህርትም ሆነ የእስከዛሬው የጋራ አቋም /ጥረት ያሳደረው ተጽዕኖ እንዲሁም ሂደቱ ያስከተለው ፖለቲካዊ አንድምታ ይበል የሚያሰኝ /አበረታች/ ለቀጣይነቱም ለሁላችንም በዓላማና ተግባር እንድንተሳሰር ወቅታዊ አገራዊ ጥሪ የሚያስተላልፍ መሆኑን በቀላሉ መረዳት ይቻላል፡፡
  1. 3. የጋራ አቋም
ጥያቄአችን ከመነሻው በምርጫ የመሣተፍ /ያለመሣተፍ ጉዳይ አልነበረም፤ ዛሬም አይደለም፡፡ ጥያቄአችን በጥቅሉ በህገ መንግስቱ መሠረት የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ተከብረው በዜጎች ይሁንታ /ድምጽ በሠላማዊ የሥልጣን ሽግግር የህግ የበላይነት የተከበረበት፤ ትክክለኛ መድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መገንባት እንዲቻል ለነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ተአማኒ፣ አሳታፊ፣ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ የውድድር ሜዳው ይስተካከል ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ ገዥው ፓርቲ የምርጫ ፖለቲካውን በቁጥጥሩ ሥር በማዋል ለቀጣይ 40 እና 50 ዓመታት በብቸኝነት አገሪቱን እገዛለሁ ለሚለው ዓላማዊ የኢብምቦን በጉዳይ ፈፃሚነት የሚጠቀምበትን ሥውር (አንዳንድ ጊዜም ግልጽ) እጁን እንዲያነሣ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተሻሻለው የምርጫ ህግ (አዋጅ ቁጥር 532/1999) አንቀጽ 7 በተሰጠው ሥልጣንና ተግባር መሠረት ኃላፊነቱን በገለልተኝነት መወጣቱን እንዲያረጋግጥ፣ በዚህም ነፃና ግልጽ የውይይት /ምክክር መድረክ በመፍጠር በዚህ ወሳኝ አገራዊ ጉዳይ ላይ በምርጫ ህጉ አንቀጽ 7(16) መሠረት እንደ ዋነኛ ባለድርሻ ያወያየን/ እንመካከርበት ነው፡፡
ስለዚህ በጥያቄአችን የተነሱ መሠረታዊ ጉዳዮች ባልተሟሉበት ማለትም ባለንበት ተጨባጭ እውነታ እንደ ፓርቲ ስለውድድር፣ እንደዜጋ ስለ መራጭነት ምዝገባ መነጋገር ለገዢው ፓርቲ የምርጫ ሴራ ይሁንታ መስጠት፣ አልፎም የምርጫ መርሆዎች እንዳይከበሩ በመተባበር በህገ መንግሥቱ መሠረት ዘላቂ የመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚደረገውን ሠላማዊ ትግልና ጥረት ወደኋላ መጎተት ነው፡፡ ይህም የለውጥ ፍላጎታችንን፣ የዓላማ አንድነታችንን፣ ጽናታችንንና ቁርጠኝነታችንን በጥያቄ ውስጥ መክተት ነው፡፡
በመሆኑም ጥያቄአችን ባልተመለሰበት ስለምርጫ ተሣትፎ ማሰብ “ተጨፈኑ ላሞኛችሁን” መቀበል ከመሆኑ በተጨማሪ ጥያቄአችንን እነርሱ ወደ ፈለጉት ደረጃ ማውረድ /ማሳነስ ነው፡፡ ስለዚህ በጋራ ይዘን ለተነሳው ጥያቄ ምርጫ ቦርድም ሆነ ገዢው ፓርቲ /መንግሥት እስከዛሬ ጆሮአቸውን ቢደፍኑም ዛሬም ጊዜ እንዳላቸው በማስረዳት ተገደው እንዲሰሙ ለማድረግ ህዝባዊ ንቅናቄ በመፍጠርና ማስተባበር የተባበረና የተቀናጀ ትግላችንን እንቀጥላለን፡፡
ይህ ማለት መቼውንም እኛ ከምርጫው ሂደት ውጪ አይደለንም፤ ማንም ውጪ ሊያደርገን አይችልም፡፡ እንደዋነኛ የምርጫው ባለድርሻ በሂደቱ ላይ ያነሣነው ጥያቄ እስኪመለስ መራጩን ህዝብ ከጎናችን በማድረግ በጥያቄአችን ያነሣናቸው ጉዳዮች መፍትሔ እንዲያገኙ እኛም በተደጋጋሚ እንደገለጽነው ወደ ሥልጣን መሸጋገሪያው ብቸና መንገዳችንን አስከፍተን በተስተካከል የመወዳደሪያ ሜዳ የመጠቀም /በምርጫ የመሣተፍ/ መብታችንን ለማስከበር የሚደረግ ትግል ነው፡፡ ለዚህ ተፈፃሚነት በአጭር ጊዜ በጋራ ማከናወን ያለብን ተግባራት
  1. ባሳለፍነው ውሳኔ መሠረት ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት መውሰድ፤
  2. እየተነጋገርንበት ላለው በትብብር የመሥራት ጉዳይ የተዘጋጀውን የመግባቢያ ሠነድ ረቂቅ በማጠናቀቅ አጽድቆ በሠነዱ መሠረት ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መግባት፤
  3. የመግባቢያ ሠነድ ረቂቅ ላይ ከሚደረገው ውይይት ጎን ለጎን ይህንን የጋራ አቋማችንን ለጉዳዩ ዋነኛ ባለቤትና ባለድርሻ አካላት ማሳወቅ፤ በተለይም ከጉዳዩ ተጠቃሚና ቀጥተኛ ባለቤት (መራጩ ህዝብ) ጋር በህዝባዊ የውይይት መድረክ መገናኘትና መወያየት፤ ናቸው፡፡
ስለሆነም መላው የአገራችን ዜጎች እንዲሁም በኢትዮጵያ አሣታፊ የመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲገነባ የበኩላቸውን ድርሻ የሚያበረክቱ አገራት፣ ዓለም አቀፋዊና አህጉራዊ ተቋማት ከጎናችን ሆነው ነፃ፣ ፍትሀዊ፣ አሣታፊ፣ ተአማኒና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ እንዲካሄድ ጥያቄዎቻችን ምላሽ ያገኙ ዘንድ ተገቢውን ተጽዕኖ በማድረግ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪያችንን አበክረን እናቀርባለን፡፡
በተባበረ ሰላማዊ ሕዝባዊ ትግል ዲሞክራሲዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት ከድርጅታችን ይልቅ ለአገራዊ የህዝብ ጉዳዮች ቅድሚያ በመስጠት በትብብር እንሰራለን!!
ጥር 07/2005 ዓ.ም
አዲስ አበባ
በአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት የተሰራጨ
maleda times | January 15, 2013 at 8:10 pm | Categories: AMHARIC NEWS | URL: http://wp.me/p2gxmh-1kB
Comment  

       

No comments:

Post a Comment