Thursday, March 13, 2014

የኛዎቹ አንቲገኖች

የሠላማዊ ትግልን ምንነት እና ሁነት በጥልቀት ያጠኑ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ወደ ጥንታዊ ግሪክ ኪናዊ- ትውፊት እስከማመላከት ይዘልቃሉ፡፡ የአንቲገንን ተግባር በምሳሌነት በማጣቀስ፡፡ በዚያ ዘመን ግሪክ በእርስ በርስ ጦርነት ትታመስ ነበር፡፡ እንዲያም ሆኖ በወቅቱ ሀገረ-ግሪክን ይገዛ የነበረው ኤዲፐስ ንጉስ፣ በእርስ በርስ ጦርነቱ የሞተ ማንኛውም ሰው አስከሬን እንዳይቀበር የሚል ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ የንጉሡ ከውሃ የቀጠነ ሕግ ያልተዋጠላት አንቲገን ግን የመጣው ይምጣ ብላ ትዕዛዙን ጣሰች፡፡ በጦርነቱ ሕይታቸው ካለፈ ሁለት ወንድሞቿ የአንዱን (የፖሊንሰስን) አስከሬን ቀበረች፡፡ በዚህም የተነሳ ተጠያቂ ሆና ንጉሡ መንበር ፊት እንድትቀርብ ተደረገ፡፡ ንጉሡም ለወጉ ያህል ቃሉን (ሕጉን) የተላለፈችበትን ምክንያት እንድታስረዳና ለቀረበባትም ክስ መከላከያ ካላት እንድታቀርብ ጠየቃት፡፡ እናም የሚከተለውን መልስ ሰጠች፡- “… ታማኝነት ለእግዚአብሔር ሕግ እንጂ ለምድራዊው ንጉስ ለአንተ ሕግ አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ሕግ ደግሞ የሞቱትን ወገኖች አስከሬን እንድንቀብር ያዛል፡፡ ስለዚህ መጠየቅ ያለብህ አንተ እንጂ እኔ አይደለሁም፤ የእግዚአብሔር ቃል የሚፃረር ሕግ ያወጣኸው አንተ ነህና፡፡…” አንቲገን ከላይ የሰጠችውን ምላሽ ብቻ ተናግራ አላበቃችም፡፡ እውነትን ተመርኩዛ ንጉሱን ባለማወላወል ተጋፈጠችው፡፡ “… ይልቅስ ከተማው በሙታን ክርፋት ተጥለቅልቆ ወረርሽኝ እንዳይከሰትና እንዳይስፋፋ ሙታኖች እንዲቀበሩ ትዕዛዝ ስጥ፡፡…” አለችው፡፡ በዚህ ቁርጠኛ ምላሿ በንዴት የጦፈው ኤዲፐስ ንጉስ ከቅጣት ሁሉ እጅግ የከፋውን የቅጣት ውሳኔ አስተላለፈባት፡፡ ሳትሞት ከነሕይወቷ እንድትቀበር ወሰነ፡፡ “በማይሻር ንጉሣዊ ቃሉ” መሰረት አንቲገን በቁም ተቀበረች፡፡ እኛስ? አሁን፤ እኛም በኤዲፐስ ንጉስ ዘመን በጥንታዊቷ ግሪክ ውስጥ ያለን ይመስለኝ ይዟል፡፡ በግልፅ “ምንም ዓይነት የመብት ጥያቄ አትጠይቁ” የሚል አዋጅ አልወጣም እንጂ፤መንግስት ምንም ነገር ላለመስማት የወሰነበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ አሁን አሁን ሳስበው መንገድ ላይ እየሄድን ጨጓራችንን ቢያመን እና ብናቃስት፣ (ለነገሩ ምን ጨጓራ አለን? ተቃጥሎ አልቋል) “የማይፈለግ ድምፅ ማሰማት” በሚል በፖሊስ ተይዘን ዘብጥያ የምንወርድ ይመስለኝ ይዟል፡፡ ለዚህ አባባሌ ምክንያት አለኝ፡፡ ከቀናት በፊት በተደረገው የሴቶች ታላቁ ሩጫ ላይ የተሳተፉ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት “አላስፈላጊ ድምፅ በማሰማት” ወይም እየሮጡ የመብት ጥያቄ በማንሳታቸው በፖሊስ ተይዘው እስርቤት መጣላቸውን ሰማሁ፡፡ አዘንኩ፡፡ እነዚህ ወጣት ሴቶች ለእኔ “አንቲገንን” ማለት ናቸው፡፡ የሚገርመው በዚህ ዘመን በግንባር ቀደምትነት የመብት ጥያቄን ከሚያነሱ ግንባር ቀደም ታጋዮች መሃል የሚበዙት እና ጎልተው የሚንቀሳቀሱት ሴቶች መሆናቸው ነው፡፡ ከእኛ ወንዶቹ በላይ ሴቶቹ “እምቢ ለመብቴ” ለማለት ቁርጠኞች መሆናቸውን ስንቶቻችን ልብ ብለን ይሆን?....(ይህንን ጉዳይ ሌላ ጊዜ በሰፊው እመለስበታለሁ) ሌላው ቀርቶ እዚህ ማህበራዊ ድረገፅ ላይ በሰከነ መንገድ በመወያየት ረገድ፤ በተለያየ መድረኮች ላይ በግንባር ቀደምትነና በቁርጠኝነት በመሳተፍ ሴቶች እህቶታቻችን ዓይነተኛ ሚና እየተጫወቱ መሆኑን አለመናገር ንፉግነት ነው፡፡ …. የሆነ ሆኖ እየሮጡ መናገር፣ እየሮጡ መብትን መጠየቅ ሊያሳስር አይገባም ባይ ነኝ፡፡ ስለዚህ የ“እኛዎቹ አንቲገኖች” (ሴት ታጋዮች) ይፈቱ፡፡ የመብትን ጥያቄ ዜጎችን በተለይም ሴት እህቶችን እና እናቶችን በማሰር ማዳፈን አይቻልም፡፡ ክብር ለሴት ታጋዮች!! .
maleda times | March 12, 2014 at 7:41 pm | URL: http://wp.me/p2gxmh-3Y2

No comments:

Post a Comment