Saturday, January 25, 2020

የአማራ ክልል ፈተናዎች እና “ጭምት” አመራሩ – ክፍል ሁለት (በመስከረም አበራ)



በሃገራችን ሩብ ምዕተ-ዓመት ያስቆጠረውን የህወሃት የበላይነት ያስወገደውን ለውጥ ተከትሎ የአማራ ክልል አዳዲስ ፈተናዎች እንደተጋረጡበት ባለፈው ሳምንት ባስነበብኩት ፅሁፍ ለመዳሰስ ሞክሬያለሁ፡፡እነዚህ ፈተናዎች በህወሃት የበላይነት ዘመን ለአማራ ህዝብ ላይ ተጋርጠው በነበሩት ፈተናዎች ላይ የተደረቡ መሆናቸው ፈተናውን ድርብርብ እና ውስብስብ ያደርገዋል፡፡የመጣው ለውጥ የአማራን ህዝብ የቆዩ ፈተናዎች በማቃለል ረገድ ያመጣው ተጨባጭ ነገር አለ ብሎ ለመናገር አያስደፍርም፡፡በአማራ ህዝብ ላይ የተቃጣው ጥቃት ኢትዮጵያን ለማጥፋት የተወረወረው ፋላፃ አካል ነው፡፡በአማራ ክልል ላይ የፈተና ዶፍ የሚያወርዱ አካላት ኢትዮጵያን እና አፈጣጠሯን የማይወዱ የፖለቲካ ሃይሎች ናቸው፡፡ይህን የደደረ ፈተና ለማቃለል ደግሞ የፈተናውን  ክብደት የሚመጥን ንቁ፣ቆራጥ፣ጥንቁቅ እና የተሰጠ አመራር ያስፈልጋል፡፡ሆኖም አማራ ክልልን የሚመሩ አመራሮች ወቅቱ የሚጠይቀውን የአመራር አቋም ይዘው ስለመገኘታቸው አፍ ሞልቶ የሚያስወራ ምልክት ያለ አይመስልም፡፡
የአማራ ክልል አስተዳዳሪዎች በህዝባቸው ልብ የሚጣልባቸው እንዳይሆኑ ያደረገ በርካታ ምክንያት አለ፡፡ የመጀመሪያው የጥራዝ ነጠቁ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ትግል የአማራን ህዝብ በጨቋኝት የፈረጀበት ደመ-ነፍሳዊ አካሄድ የወለደው አማራውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ መርገም ሁሉ ምንጭ አድርጎ የማየቱ ትንተና ያመጣው ነገር ነው፡፡ ይህ አማራውን ጨቋኝ አድርጎ የማየቱ ነገር ህወሃት የተባለው የባሰበት ጥራዝ ነጠቅ ደደቢት ከመሸገበት፣ አዲስ አበባ እስከ ገባበት፣ ከዛም ፈላጭ ቆራጭ ሆኖ ግማሽ ምዕተ አመት ስልጣን ላይ በተወዘተበት ዘመን ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ህወሃት ጌታ ሆኖ ኢትዮጵያን ሲያሾር በኖረበት ዘመን ካሰማራቸው ሶስት የእህት አምስት የአጋር ድርጅት ሎሌዎች መሃል አንዱ የአማራ ክልልን የሚያስተዳደርው ብአዴን ነበር፡፡
ሁሉም የአባል/አጋር ፓርቲ ሎሌዎች በአሳዛኝ ራስን የማከራየት ጎስቋላ ህይወት ውስጥ የነበሩ ቢሆኑም የብአዴንን ለየት የሚያደርገው በራሱ ህዝብ ላይ የተቃጣውን ጦርነት ሊያጋፍር የወጣ ሎሌ መሆኑ ነው፡፡ይህ ቡድን ከሎሌነቱ የባሰ ሌላ ፈተና ነበረበት፡፡ ይኽውም “እንደ ወጣበት ህዝብ ትምክህተኛ አለመሆኑን” ለጌታ ህወሃት የማስመስከር የማያልቅ ስራ ነበር፡፡ይህን ለማስመከር ደግሞ ህወሃት በአማራ ህዝብ ላይ የሚያወርደውን ሁለንተናዊ መከራ ዝቅ ሲል ባላየ ማለፍ ከፍ ሲል ደግሞ ከህወሃት ጋር ተደርቦ የራስን ህዝብ ልብስ አስወልቆ በእሾህ ለበቅ መለብለብ ያስፈልግ ነበር፡፡ይህን በማድረግ የብዴን ሹማንነት “አማራ በመሆናቸው ምክንያት ከዘር የወረሱትን  የትምክህተኝነት ሃጢያት” የማራገፋቸውን ለጌታ ህወሃት ያስመሰክሩ ነበር፡፡ይህ ከሩብ ምዕተ-ዓመት በላይ ከብአዴን ሹማምንት ጋር አብሮ የኖረ አባዜ እንዲህ  በቀላሉ ትቷቸው ሊሄድ አይችልምና ዛሬም ለህዝባቸው ለመቆም ወገባቸውን ሳይዘው አልቀረም፡፡
ይህ ድክመት ከብአዴን ሹማንምንት ያለፈ ታሪክ ብቻ የሚቀዳ አይደለም፡፡ይልቅስ ከላይ ከፍ ብሎ እንደተቀመጠው ከነጥቆ በረሩ የኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ ዘመን ጀምሮ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ንፋስ ውስጥ አማራውን ጨቋኝ አድርጎ የመሳሉ ነገር ዛሬ ድረስ ተሻግሮ ክልሉን የሚመሩ ባለስልጣናት ለህዝባቸው እንዳይሰሩ ቀላል የማይባል ተፅዕኖ ሳያስከትል አልቀረም፡፡ይህም ማለት የአማራ ክልልን የሚመሩ ባለስልጣናት ለህዝባቸው የመቆርቆር ነገር ካሳዩ “የቆየ ትምክህታቸውን ሊመልሱ፣የቀድሞውን ስርዓት ሊያመጡ” የሚል ዜማ ይከተላቸዋል፡፡ ይህ ነገር የአማራ ክልል አመራሮች ከሌላው በተለየ “ጭምት” እንዲሆኑ ሳያደርግ አልቀረም፡፡ይህን ነገር ለመስበር ደግሞ የክልሉ አመራሮች በህወሃት ዘመን በከፍተኛ የስነልቦና ስልበት ውስጥ የቆዩ በመሆናቸው ዛሬ ብድግ ብለው በራሱ የሚተማመን፣የሚቆምለት መርህ ያለው፣የፖለቲካ ተደራዳሪነትን ካርዶችን አሰላስሎ ሰብስቦ አጀንዳ አስቀማጭ ሊሆኑ አይችሉም-በጥብቅ ሰንሰለት ታስሮ የኖረ ምርኮኛ ሰንሰለቱ ቢፈታለትም ቶሎ እጁን ማዘዝ እንደማይችል ሁሉ!
ይህ ልማድ ግን ለአማራ ህዝብ ደህንነትም ሆነ ለኢትዮጵያ ህልውና ሲባል ነገ ዛሬ ሳይባል መወገድ ያለበት ልማድ ነው፡፡አማራ ክልልን የሚመሩ መሪዎች “ጭምትነታቸውን” ማቆም አለባቸው፡፡በክልሉ ላይ የተደቀነው ፈተና በትናንቱ የፖለቲካ ልማድ የሚወጡት አይደለም፤ለአፍታም የሚያስተኛ አይደለምና ወገብ ጠበቅ አድርጎ መስራት ያስፈልጋል፡፡ እዚህ ላይ “የሚሰራው ስራ ምንድን ነው?” የሚል ተገቢ ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡የሚሰራው በርካታ ስራ ቢሆንም እኔ የታየኝን ላስቀምጥ፡፡
ነቀፌታን ማስወገድ
ለውጥ መጣ ከተባለ ወዲህ በተለይ ወያኔ እንኳን ወደመረሻው አካባቢ ረስቶት የነበረውን የአማራን ህዝብ የማብጠልጠል ነገር በተለይ በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ በግልፅ በአደባባይ እየተቀነቀነ ይገኛል፡፡ይህ የአማራን ህዝብ የማብጠልጠያው መግቢያ በር “ነፍጠኛ” የሚለው አማራው ሊያፍርበት የማይችለው፣ይልቅስ የሚኮራበት ስም ነው፡፡ሆኖም ዋናው ጉዳይ ያለው አማራው “ነፍጠኛ” ለሚለው ስም  የሚሰጠው ትርጉም ላይ አይደለም፡፡ዋናው ጉዳይ ያለው ሌሎች ለዚህ ስም የሚሰጡት ትርጉም ላይ ነው፡፡ የመከፋፈል ካህኑ መለስ ዜናዊ “ነፍጠኛ” የሚለውን ቃል አማራው ከሚያውቀው በተለየ ሁኔታ ለካድሬዎቹ ሲያሰለጥን ኖሯል፡፡አማራውን ከኢትዮጵያ እኩል የሚጠሉ አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞችም ሆኑ የሌላ ዘውግ ፖለቲከኞች “ነፍጠኛ” ለሚለው ስም ያላቸው ትርጓሜ ከመለስ ዜናዊ ጥራዝ ነጠቅ ካድሬዎች የተለየ አይደለም፡፡
በነዚህ አካላት ትርጉም “ነፍጠኛ” ማለት ቅኝ ገዥ፣የሰው ባህል ጨፍላቂ፣የሰው መሬት ቀማኛ፣በኢትዮጵያ ብሄረሰቦች ላይ የዘር ማጥፋት ያደረገ ጨካኝ ማለት ነው፡፡በዚህ እሳቤ መሰረት አሁን በህይወት ያሉ፣ የዚህ ነፍጠኛ የተባለው “ጭራቅ” ልጆች ደግሞ አሁን ላይ የአባቶቻቸውን ሃጢያት ደሞዝ ማግኘት አለባቸው የሚል የማይናወጥ አቋም አለ፡፡ይህ እሳቤ ነው በኢትዮጵያ ዳርቻ ላሉ አማሮች በህይወት የመኖር ስጋት፣ይህ እሳቤ ነው አማራ ክልልን በየአጋጣሚው የማሳቀል ምክንያት፣ይህ እይታ ነው ጊዜ እና ቦታ ሳያስመርጥ ከባስልጣን እስከ መደዴ የፖለቲካ ንግግር ማሳመሪያው አማራን ማንጓጠጥ አድርጎ እንዲታሰብ ያደረገው፡፡ችግሩ አማራውን በማንጓጠጥ የሚቆም ቢሆን ኖሮ በአመዛኙ  የአማራ ህዝብ ካለው ጠንካራ የስነልቦና ውቅር አንፃር አሳሳቢ አይሆንም ነበር፡፡ ዋናው ችግር ይህ እሳቤ ወደ ተግባር ተቀይሮ እጅ እና እግር፣ጥፍር እና ጥርስ አውጥቶ አማራውን እና የአማራ የተባለን ነገር ሁሉ ሊውጥ መንደርደሩ ነው፡፡ይህ አደጋ በቀጥተኛ ቋንቋ ሲገለፅ ከክልሉ ውጭ የሚኖረው አማራ በተለይ በከፍተኛ የእልቂት ስጋት ውስጥ መገኘቱ ነው፡፡
ይህን ችግር ለማቃለል ክልሉን ከሚመሩት መኳንንት የቀረበ ሰው የለም፡፡ችግሩን ለማቃለል በክልሉ ሹማንት ሊደረግ የሚገባው ቀዳሚው ነገር ከክልሉ ውጭ ለሚኖረው አማራ ሃላፊነት ያለባቸው መሆኑን መረዳት ነው፡፡ይህን ከተረዱ በኋላ በመጀመሪያ ከእራሳቸው ፓርቲ ጓዶች የሚመጣውን እልቂት የሚጠራ የአደባባይ ንግግር በአንክሮ ተመልክቶ በጠንካራ ወገብ መፋለም ነው፡፡ይህ ማለት አንድ ሁለት ቀን ተደርጎ የሚረሳ የሁለት ካድሬዎች የፌስ ቡክ ንትርክ ማለት አይደለም፡፡ከዛ ያለፈ ነገር ያስፈልጋል፡፡ባለቤት ካልናቁ አጥር አይነቀነቅምና “በአንድ ፓርቲ ጥላስር ያለ አጋር ተዝናንትቶ በአደባባይ የምመራውን ህዝብ የሚወርፈው እኔን እንዴት ቢያየኝ ነው?” ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፤በግማሽ አይን መታየት ጥሩ ነገር አለመሆኑን ለራስ መንገር ያስፈልጋል፣መከባበር የሌለበት የሽንፈት ህብረት ወንዝ እንደማያሸግር አምኖ ለዚሁ መስራት ያስፈልጋል፡፡ ይህን ገቢራዊ ለማድረግ በፓርቲ ስብሰባዎች፣በፖለቲካዊ ግንኙነቶች ወቅት አጥንት ለብሶ መቆምን ይጠይቃል፡፡
የቤትን እርግጫ አደብ ካስያዙ በኋላ የሚቀጥለው ከወጭ የሚመጣውን ውረፋ መቋቋም ነው፡፡ከውጭ የሚመጣው ውረፋ ከዘውግ ብሄርተኞች የሚሰነዘር የአማራውን ህዝብ ህይወት እጅግ ለከፋ አደጋ የሚያጋልጥ፣የማምለክ መብቱን የሚጥስ በአጠቃላይ አማራነትን የሞት ምልክት የሚያደርግ እጅግ አደገኛ ነገር እየሆነ መጥቷል፡፡ይህን ነገር ዝም ብሎ ማየት የአማራ ህዝብ ፍትህን ከእጁ እንዲያገኝ መገፋፋት፣ሃገራችንንም ወደ አላስፈላጊ ትርምስ መክተት ነው፡፡ቤኒሻንጉል ላይ የአማራ ህፃናት ሳይቀሩ በቀስት ሲሰነጠቁ ክልሉን የሚመራው አመራር ችላ በማለቱ የሆነው ነገር የሚታወቅ ነው፡፡ያን መሰል ድርጊት አሁንም እንዳይደገም መፍትሄውን ማምጣት የሚችለው መራሩ ነው፡፡መፍትሔ ማምጣት ማለት ደግሞ ህፃን ልጅን እንኳን የማያሳምን “እየተከታተልን ነው፣ጎጅ ባህል ስለሆነ ነው፣እልባት ለመስጠት አቅጣጫ ተቀምጧል” የሚል አሰልች ፕሮፖጋንዳ መደርደር አይደለም፡፡የአማራ ህዝብ በሚገደልበት ክልል ሁሉ ክልሉን የሚመሩ ባለስልጣናት ችልታ ወይ እገዛ አብሮ አለ፡፡ይህ ቅድም ከላይ የተነሳው መለስ ዜናዊ በካድሬዎቹ ውስጥ አስርጎት የሄደው ስልጠና ውጤት ነው፡፡ ስለዚህ አማራው በሚታረድበት ጥጋጥግ ያሉ አመራሮች ሁሉ ሃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው የሚጠየቁበትን መንገድ ጠንከር ብሎ መጠየቅ የአማራ መኳንንት ፋንታ ነው፡፡በየሚያስተዳድሩት ክልል  አማሮች ሲታረዱ፣ቤታቸው ሲቃጠል፣እምነት ቦታቸው ዶግ አመድ ሲሆን ዝም የሚሉ በብልፅግና ፓርቲ ስር ያሉ አመራሮች አማራ የክልልን ከሚመሩ ጓዶቻቸው ይልቅ ለነጃዋር የሚቀርብ ስነ-ልቦና ያላቸው እንደማይጠፉ ግልፅ ነው፡፡እነዚህን አመራሮች ተከታትሎ መገዳደር የአማራ መኳንንት ስራ ነው፡፡በአጠቃላይ የአማራ ህዝብ ስቃይ ነፍጠኛ የሚለውን ስም እና ተከትሎት የሚመጣውን እሳቤ ተንተርሶ የሚመጣ ነውና ይህን የነቀፌታ እሳቤ በአደባባይ ማፀባረቅ ቀለል ተብሎ የሚነገር መሆኑን ማስቆም ግድ ነው፡፡ሌሎች ብሄረሰቦች ሊባሉ የማይፈልጉትን ስም ማስወገድ የቻሉት ወከልናችሁ የሚሏቸው ልጆቻቸው ተግተው ስለሰሩ ነው፡፡ “ለሌሎች ህዝቦች የሚደረገው ጥንቃቄ ለእኔ ህዝብ የማይደረገው እኔ ምን ቢጎድለኝ ነው?” ብሎ ማሰብ ከባድ ነገር አይደለም!
ራስን በትክክል መግለፅ
የዘውግ ፖለቲከኞች የአማራን ክልልን በውስጡ ያሉ ብሄረሰቦችን መብት ካለማክበር እስከ ዘር ማጥፋት ወንጀል መፈፀም ድረስ በደረሰ የበሬ ወለደ ክስ እንደሚያብጠለጥሉ የሚታወቅ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ለዚህ ዘመቻ ምንም የሚመልሰው ነገር ስለሌለ የሃሰት ክሱ የብቸኛ እውነትነትን ማማ ተቆናጦ ቁጭ ብሏል፡፡ ዛሬ አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያውቀው የቅማንት ህዝብ በህገመግስቱ በተደነገገው መሰረት  ብሄረሰብ የሚያስብለው የተለየ ቋንቋ ሳይናገር፣ አማርኛ እየተናገረ የልዩ ብሄረሰብ አስተዳደር የተሰጠው ብቸኛ ህዝብ መሆኑን ሳይሆን ጥያቄው ታፍኖ በአማራ ልዩ ሃይል የዘር ማጥፋት እየተደረገበት እንደሆነ ነው፡፡ይህን የሚያራግበውን ሚዲያ በህግ ተጠያቂ ማድረግ ቀርቶ የተለያዩ ሚዲያዎችን ተጠቅሞ የአማራ ክልል ለቅማነት ህዝብ ያደረገውን እላፊ መብት የማክበር ፈለግ የማስተዋወቅ ስራ እንኳን መስራት አልተቻለም፡፡ ስለዚህ ሃሰቱ እውነት አክሎ በአማራ ህዝብ ጠላቶች የፕሮፖጋንዳ ከበሮ ይመታበታል፡፡
የአማራ ክልል የሚብጠለጠልበትን የብሄረሰቦች መብት የመደፍጠጥ የሃሰት ወሬ ውድቅ የሚያደርገው የቅማንት ጥያቄ ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ ለኦሮሞ፣ለአገው ህዝቦች የተሰጠው የራስን በራስ የማስተዳደር መብትም ሌላው ምስክር ነው፡፡ የአማራ ክልልን በብሄረሰቦች መብት ጨፍላቂነት የሚከሱ ሰዎች የእኛ በሚሉት ክልል በአማራው፣በጋሞው፣በጉራጌው ወላይታው፣ጌዲኦው ላይ  በአደባባይ በማይክራፎን ግልፅ የዘር ማጥፋት አዋጅ የሚታወጅበት ነው፡፡ይህን ጠቅሶ ታገሱ የሚል እውነታውን የሚያሳይ ያልተጋነነ፣ፕሮፖጋንዳ ያልሆነ፣ህዝብን ከህዝብ የማያጋጭ ግን ደግሞ እውነቱን የሚያሳይ የሚዲያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ነገር ካልተሰራ እነዚህን አካላት ከአማራው ህዝብ አናት ላይ ማውረድ አይቻልም፡፡ይህን ለማድረግ ደግሞ የአማራን ክልል የሚመሩት አመራሮች ቀዳሚ መሆን አለባቸው፡፡ በተግባር ሲታይ ግን ይህን በማድረጉ ረገድ አንድ የፌስቡክ ገፅ ያለው ግለሰብ የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረገ ይመስላል፡፡ ይህ የግለሰቦች የማህበራዊ ደረ-ገፅ እንቅስቃሴ ደግሞ ደምፍላት ያለው፣ሙሉ እውነታውን ሊያቀርብም የማይችል፣ጭራሽ ግጭቱን የሚያካርር በመሆኑ ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚበልጥ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ የክልሉ መንግስት ነገ ዛሬ ሳይል የክልሉን ተጨባጭ እውነታ ለኢትዮጵያ ህዝብ በማቅረብ ሃሰትን ቦታ ማስለቀቅ ይጠበቅበታል፡፡
ያደረ አጀንዳን የመግለጥ ስራ
በአሁኑ ወቅት እየተጋጋለ የመጣው አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኝነት ጎራ ከህወሃት ውድቀት ወዲህ የታየው ለውጥ በኦሮሞ ልጆች ትግል የመጣ እንደሆነ ያምናሉ፡፡ስለሆነም ህወሃት ያደርግ እንደነበረው የትግል ጀብዷቸውን እየተረኩ የህወሃት የበላይነትን በኦሮሞ ሊሂቃን የበላይነት ለመተካት ይሻሉ፡፡ ሆኖም የኢትዮጵያ ህዝብ ንቃት ከዚህ አልፎ በመሄዱ ምኞታቸው ስጋ ሊለብስ አልቻለም፡፡ይልቅስ ኦሮሞ ብቻ ታግሎ እንዳመጣው የሚያምኑት ለውጥ የዘረጋው ፖለቲካዊ ዘይቤ እያሳካ ያለው  ነፍጠኛ/አሃዳዊ እያሉ በተለያየ ስም የሚጠሩትን የአማራን ህዝብ ፖለቲካዊ እሳቤ እንደሆነ ያምናሉ፤አምነውም ይብሰለሰላሉ፡፡በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ጎራ እሳቤ መሰረት ኢትዮጵያ የተሰራችበትን እውነት ተቀብሎ፣የሚታረመውን አርሞ፣አንድነቷ ተጠብቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ፖለቲካ የምትሄድበትን መንገድ መተለም የአማራ ብቻ ናፍቆት ነው፡፡ለዚህ ነው ከኦሮሞ  ህዝብ የወጣውን ጠቅላይ ሚንስትር አብይን አፄ ምኒልክን በሚጠሉበት ጥላቻ አምርረው የሚጠሉት፣በአማራ ጉዳይ አስፈፃሚነት የሚከሱት፡፡ይህን ሁሉ ያመጣው አሁን የመጣው ለውጥ የመጣው በኦሮሞ ልጆች ትግል ሆኖ ሳለ የጠቀመው ግን አማራን ነው ብሎ ከማሰብ ነው፡፡
ይህን የተንሸዋረረ እሳቤ ማስተካከል አሁንም በብልፅግና ፓርቲ ውስጥ ያሉ የአማራ መኳንንት ተቀዳሚ ተግባር መሆን አለበት፡፡የማስተካከያ ስራው መጀመር ያለበት ደግሞ የመጣው ለውጥ አክራሪ ብሄርተኞች እንደሚያስቡት ለአማራው የተለየ ያመጣው ነገር እንደሌለ ነው፤ይልቅስ የአማራህዝብ ሃገሩ በለውጥ ምጥ እንዳትሞት ፣ለውጡ እስኪረጋ ድረስ ጊዜ በመስጠት፣ከሁሉ በላይ ኢትዮጵያን በማስቀደሙ ብቻ በይደር ያስቀመጣቸው በርካታ አጀንዳዎች እንዳሉት ማሳወቅ ነው፡፡በይደር የተቀመጡ አጀንዳዎችን ወደማሳቱ ከማለፌ በፊት ግን ሌላ አበይት ነጥብ ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ይኽውም ጠ/ሚ አብይን ወደ ስልጣን ያመጣው ለውጥ ሲረገዝም ሆነ ሲወለድ አማራው በአቶ ደመቀ መኮንን በኩል ከማንም በላይ ለስልጣን ቅርብ ሆኖ ሳለ ለስልጣን ልሙት ሳይል ሃገር የሚያረጋጋው መንገድ ስልጣን መያዙ ስላልመሰለው ስልጣኑ ወደ ኦሮሞ ተወላጁ ዶ/ር አብይ እንዲዞር አድርጓል፡፡ እዚህ ውስጥ ብዙ ትርጉም አለ!
ይህን ትርጉም ለማወቅ የሃገር አጀንዳ ከዘውግ አጀንዳ ዘለግ እንደሚል መረዳትን ይጠይቃል፡፡ ይህን ያደረገ ሰው ናፍቆቱ ገዘፍ ያለው ሃገር የማዳን ተግባር እንጅ የመንደር ልፊያ እንዳልሆነ የሚገባው የሃገርን ትርጉም የሚያውቅ ብቻ ነው፡፡ጠ/ሚ አብይ ከገዛ የዘውጉ ሰዎች ሰባት ጦር የሚወረወርበት ይህ የገባው ሰው ስለሆነ ነው፡፡ጠ/ሚው የሚጠበቅበትን ያህል ሃገር የማረጋጋት ስራ እንዳይሰራ እግር ተወርች የታሰረውም በዚሁ እሳቤ ተሸካሚ የዘውጉም፣የፓርቲውም መካከለኛ እና ዝቅተኛ  ሹመኞች፣የህግ /የፀጥታ አካላት ህቡዕ ስራ ነው፡፡
ስልጣን ላይ ልሙት ሳይል ስልጣን አሳልፎ የሰጠው የአማራው ናፍቆት ሃገር ማዳን ነበር፡፡ የዚህ ስራ ትክክለኛ ትርጉም የሚገባው ግን ለሃገር ግድ የሚለው ብቻ ስለሆነ ክልል እና ሃገር የተሳከረባቸው ሰዎች የሰጡት ትርጉም ሌላ ሆነ፡፡ ስልጣንን አሳልፎ መስጠት ማጉድል መሆኑ ቀርቶ ማትረፍ ተደርጎ ተተረጎመ፡፡በታሪክ ለኢትዮጵያ ሲሞቱ የነበሩ ኦሮሞ አርበኞችን ለአማራ ንጉስ ብለው ነው ወደ ጦርሜዳ ሄደው ቀኝ ገዥን የተፋለሙት ሲሉ የኖሩት የኦሮሞ ብሄርተኞች አሁን የሃገሪቱን የመጨረሻ ስልጣን የያዘው ኦሮሞው አብይ ሲሆንም ኢትዮጵያን የሚለው በስሩ ላሉ አማሮች ተገዝቶ እንደሆነ ሲናገሩ አያፍሩም፡፡ስለዚህ የአማራ መኳንንት በመጣው ለውጥ ሃገር ያሰነበቱ መስሏቸው ሳይከራከሩ ስልጣን አሳልፈው እንደሰጡ፣በዚህም መላው አማራ ከማንም በላይ ደስ እንዳለው ማሳሰብ ሳይስፈልጋቸው አልቀረም፡፡ለዚህ ለውጥ መምጣት የብአዴን ባለስለጣናት ከህወሃት ጋር ያደረጉትን ትንቅንቅ መግለፅ ቢቻልም በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ዘንድ እየበዛ የመጣውን የብቸኛ ጀግንነት አጉል ቀንድ ሊሞርደው ይችላል፡፡
ከዚህ ቀጥሎ የሚመጣው የአማራ ፖለቲከኞችም ሆነ ህዝቡ ኢትዮጵያ ከለውጥ ነውጥ እስክትድን በእናት ሃገራቸው ህመም ላይ ሌላ ራስ ምታት ላለመጨመር ሲሉ ያሳደሯቸው አጀንዳዎች እንዳሉ ማሳወቅ ነው፡፡ይህን ማድረጉ ለውጡ ለአማራ የተለየ ቱርፋ ያመጣ ለሚመስላቸው አካላት እንዲረጋጉ በማድረግ በኩል ጥቅም ይኖረዋል፡፡ከነዚህ አጀንዳዎች አንዱ ወልቃይትን ጨምሮ ሌሎች ከጎንደር ግዛት ላይ በህወሃት ተዘርፈው የተወሰዱ ለም መሬቶች፣እነዚህን ለም መሬቶች ለመወሰድ ሲል ህወሃት በአማራ ህዝብ ላየ የፈፀማቸው ዘር ማጥፋቶች፣ሰው ሰራሽ የዲሞግራፊ ለውጦች፣የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ጉዳይ ነው፡፡ሌላው ቀርቶ ከዚሀ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ከጎንደር ግዛቶች እየታፈኑ ተወስደው ትግራይ እስርቤት ስለታሰሩ እስረኞች ቢነሳ ብዙ ጉድ አለ!
እንደሚታወቀው በደቡብ ክልል ያለው የሲዳማ ዞን ልሂቃን  ወደ ክልል ለማደግ የሚያደርጉትን ትግል አጧጡፈው ያነሱት ህወሃትን ባስወገደው ለውጥ ማግስት ነው፡፡ ይህን ትግል ሲያደርጉ ዛሬውኑ ጥያቄያችን ይመለስ የሚል ፋታ የሌለው ትግል አድርገው፣በርካታ ነዋይ ፈሰስ ተደርጎ ሪፈረንደም አስደርገው ጥያቄያቸው አንድም ሳይሸረፍ መቶ በመቶ መልስ አግኝቷል፡፡ የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄም በአማራ ህዝብ ዘንድ ከዚህ ያነሰ አንገብጋቢነት ያለው ነገር አይደለም፡፡ነገር ግን ከህወሃት ጋር ጠመንጃ እስከመማዘዝ ደርሶ የነበረው የወልቃይትማንነት ኮሚቴ ለውጡን ተከትሎ የመረጋጋት ዝንባሌ አሳይቷል፡፡ ይህ የሆነው የምንወዳት ሃገራችን ባለባት ህመም ላይ ሌላ ህመም ጨምሮ ሞቷን ላለማፋጠን ሲባል እንጅ አማራው በወልቃይት ጉዳይ ላይ የደረሰበት መከራ ቀላል ሆኖ ወይም ለወጡ ጥያቄውን መልሶለት አይደለም፡፡
ሌላው አጀንዳ በአማራው ህዝብ ቁጥር ላይ ያለው ጥያቄ ነው፡፡እንደሚታወቀው ህወሃት አማራውን ለማሳነስ ካለው አምሮት የተነሳ 2.8 ሚሊዮን አማራ የገባበት ጠፋ ሲል በአደባባ ተናግሯል፡፡ይህ የቁጥር መቀነስ ስትራቴጅ አማራው በፓርላማ ያለውን ወንበር ለማሳነስ፣ለክልሉ የሚመደበውን በጀት ለመቁረጥ፣የህዝቡን የፖለቲካ ተደራዳሪነት ግዝፈት ለመቀነስ የተደረገ የህወሃት የዝቅተኝት ስነልቦና የወለደው አካሄድ ነው፡፡ይህ የህዝብ ቁጥር ጉድለት አማራው ሁሉ ይሁን ብሎ የተቀበለው ጉዳይ አይደለም፡፡ ይልቅስ ሃገርን በማስቀደም የተተወ ነገር እንጅ! ሐገርን ባያስቀድም ኖሮ ይህ ሁሉ ህዝብ የገባበት ጠፋ የተባለው የአማራ ህዝብ የህዝብ ቆጠራ ተደርጎ ሎች እንደሚሉት “በቁመናየ ልክ ወንበር ካልተደለደለልኝ ምርጫ ውስጥ አልገባም” በማለት ሃገር የማመሱን ረብሻ መቀላቀል ይችል ነበር፡፡ህዝብ ቆጠራው ቢቀር እንኳን ጠፋ የተባለው ህዝብ ተደምሮ አሁን ባለኝ ህዝብ ቁጥር ላይ ይደመርልኝ ማለት ይቻላል፡፡ግን አልተደረገም፤አልተደረገም ማለት ግን ጥያቄ የለም፤እንደሚታሰበውም ለውጡ ለአማራዊ ፍላጎት የቆመ ስለሆነ አማራው ደስ ብሎት ዝም አለ ማለት አይደለም፡፡ይልቅስ አማራው ኢትዮጵያን የሚለው ከጉድለቱ ጋር ጭምር በመሆኑ ነው፡፡ይህን አስረግጦ ማስረዳት ደግሞ የአማራ መኳንንት ስራ ነው፡፡ ካልሆነ ሃገር ባልሆነ ተረክ ስትታመስ መክረሟ ነው፡፡
እያዚም ቤት እሳት እንዳለ ማሳሰብ
የአማራን ክልል በእጅ አዙር እያመሰ ያለው የቅማንትን ጥያቄ ተገን አድርጎ ከዘውግ ፖለቲከኞች የሚነሳው ተግዳሮት ነው፡፡ የዚህ ተግዳሮት ፊት አውራሪ ህወሃት ስትሆን ቀጣዩ ደግሞ ህወሃት የእስትራቴጅክ አጋሩ እንደሆነ በአደባባይ የመሰከረው የጃዋር ካምፕ ነው፡፡በተለይ ህወሃት የቅማንትን ጉዳይ ያለ ይሉኝታ የገባበት ከመሆኑ ብዛት የቅማንት ኮሚቴ እያለ ለሚጠራቸው ስብስቦች መቀሌ ቢሮ እስከመስጠት ደርሷል፡፡ በዚሁ ኮሚቴ ስም ታጣቂ እያስገባ የአማራ ክልልን የሚያምሰው ነገርም የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ ህወሃት ይህን የሚያደርገው የቅማንት ህዝብ የትግሬ ማንነት አለኝ ባላለበት ሁኔታ ነው፡፡በአንፃሩ የትግራይ ክልል አማራ ነኝ የሚሉ የወልቃይት ህዝቦች እና ወደ አማራ ክልል መካለል እንፈልጋለን የሚሉ የራያ ህዝቦች  ያሉበትን መሬት በጉልበት ዘርፎ ወስዶ፣ሰዎቹን መብታቸውን ረግቶ በግዞት እያኖረ ነው፡፡
ይህን ህወሃት መራሹ የትግራይ ክልል አስተዳደር የሚያደርገውን ግፍ ለመታገል የወጡ የወልቃይት ማንነት እና የራያ ማንነት ኮሚቴዎች ግን ወደ ግዛቱ እንካለል ከሚሉለት የአማራ ክልል አስተዳደር ይህ ነው የሚባል እርዳታ አግኝተው አያውቁም፡፡የትግራይ ክልል አስተዳደር ምንም በማይመለከተው የቅማንት ማንነት ኮሚቴ ውስጥ ይህን ያህል የወሳኝነት ሚና ሲወስድ የአማራ ክልል አማራ ነኝ ለሚሉ ግን ደግሞ በህወሃት ከባድ ቀንበር ስር ላሉ ህዝቦች ይህ ነው የሚባል እርዳታ ያለማድረጉ የመፋዘዙ እንጅ የብልህነቱ ምልክት ሆኖ አይታየኝም፡፡በርግጥ ህወሃት በአማራ ክልል ላይ እንደሚያደርገው የአማራ ክልል ሹማምንትም ወደ ትግራይ ክልል ታጣቂ እያሰረጉ ማተራመስ ልክ መንገድ አይደለም፡፡ከዚህ በመለስ ግን አማራ ነን በማለታቸው አበሳ ለሚያዩ ህዝቦች ድጋፍ ማሳየት ተገቢ ነገር ነው፡፡ይህ ዋናው ነገር ሆኖ እግረ መንገዱን ለህወሃትም እዚያም ቤት እሳት አለ የሚል መልዕክት መስጠቱ አይቀርም፡፡ ይህ ደግሞ የትግራይ ክልል አስተዳደር የራሱ መታወቂያ የሆነውን የህዝቦች መብት መደፍጠጥ ወደ አማራ ክልል የማላከክ ፕሮፖጋንዳውንም ሆነ ወደ አማራ ክልል የሚልከውን ፈተና ለመቀነስ ይረዳል፡፡

Monday, September 30, 2019

ማንነት ሲጋለጥ ታምራት ታረቀኝ 1999 ዓ.ም [ከመዐሕድ እስከ ቅንጅት] የልደቱ አያሌው ሴራ



"ይህን መፅሃፍ በማንበብ ስለ ልደቱ አያሌው ማንነት ለብዙ አመታት በቅርብ ከሚያውቀው ሰው ለመረዳት በመቻሌ ተደስቻለሁ። መፅሁፉ ስለ ልደቱ የነበሩኝን ጥርጣሬዎች ይበልጥ አረጋግጦልኛል።

አሁን ስለ ልደቱ ያለኝ ግንዛቤ ቀደም ብሎ ቢኖረኝ ኖሮ የኢዴአፓ-መድህን አባል ባልሆንኩ ፣ የአቶ ልደቱና መሰሎቻቸው መጠቀሚያ ባልሆንሁ ነበር።
በመፅሀፉ አንባቢያን ስለ ልደቱ ይበልጥ እንዲያውቁ በማድረጉ አቶ ታምራትን በጣም አመሰግናለሁ።
>>
ዶ/ር ኃይሉ አርአያ
<<
እንዴት አታምነንም? ቃለ ጉባኤ ሰነድ አይደለም ወይ? ይህንንም አላምንም ካልክ አዚሁ እንፈርምልሃለን። የብዕር ፊርማችንንም አላምንም ካልክ ጣታችንን ቀለም እየነከርን እንፈርምልሃለን ፣ ይህንንም አላምን ካልክ ጣታችንን እያደማን በደማችን እርምልሃለን።
>>
ከመዕሃፉ የተወሰደ
(የቅንጅት አመራሮች ዶ/ር ኃይሉ እና ዶ/ር አድማሱ)
--------------------------------------
"ልደቱ አያሌው አይበቃኸም?"
(በታምራት ታረቀኝ)
===================
በድንገተኛ ስሜት ተስቤ ኢ ኤን ኤን ቲቪ ላይ የሰማሁት የቀድሞ ወዳጄ ቃለ ምልልስ በዝምታ የማይታለፍ ሆኖብኝ የጀመርኩት ጽሁፍ ትውስታ ትውስታን እየቀሰቀሰ ለዚህ ለክፍል ሁለት አድርሶኛል፡፡ ዋና ዋናዎቹን ብቻ በማንሳት በዚሁ ለመቋጨት እሞክራለሁ፡፡
1- እኛ፤ ንግግሩ በሙሉ እኛ ነው፤ እኛ የወል መጠሪያ እንደመሆኑ ለብዙ ነገር ያመቻል፡፡ ስለሆነም ልደቱ እኛ የሚላቸው ኢዴአፓ መድህንን ወክለው የቅንጅት ሥራ አስፈጻሚ ሆነው የነበሩትን 5 ሰዎች፤ የም/ቤት አባል የነበሩትን 18 ሰዎች ወይንስ ከውህደት በፊት የነበረውን የኢዴአፓ መድህን ሥራ አስፈጻሚና ምክር ቤት አባላት ወይንስ ከውህደት በኋላ ከቅንጅት አፈንግጦ በእሱ ሊቀመንበርነት የቀጠለውን አመራር፡፡ እኛ ሲል ብቻየን አልነበርኩም ማለት ነውና እኛ የሚለው መሸፈኛ መገለጥ ይኖርበታል፡፡ አሁን ደግሞ በዶ/ር ጫኔ እና በእሱ መካከል ክፍፍሉ ለይቶለት ኢዴፓን አፍርሰነዋል ብሎ አውጇል፡፡ እናም ለአስር አመት ሙል እኛ ሲል እነማንን ጨምሮ እንደሆነ መታወቅ አለበት፡፡
2- በወቅቱ አቋማችንን ለማስረዳት ሚዲያ አልነበረንም፡፡በምርጫ 97 ወቅት ለአቅመ ፖለቲካ የደረሳችሁ ወገኖች ሁሉ ለአፍታ በአይነ ልቦና መለስ በሉና 1998 ዓ.ም አስታውሱ፡፡ አየቅንጅት አመራሮች እስር ቤት ሆነው ከእስር የተረፉትም እንኳን አደባባይ ወጥተው ሊናገሩ በየቤታቸው ለመኖር ምጥ በሆነበት እና ማንም መልስ የሚሰጠው ባልነበረበት ወቅት በወቅቱ በነበሩት የመንግስት መገናኛ ብዙኃን እንደልቡ ሲጠቀም አልነበረምን፡፡ እኔ እስር ቤት ሆኘ አየውና እሰማው ነበርና ሌላው ቢቀር ሁለት ነገሮች አይረሱኝም፡፡ አንደኛው ዛሬም ድረስ እንደሚያደርገው ራሱን ነጻ አድርጎ እስር ቤት ያነበሩትን አመራሮች ይወነጅል የነበረበት ሁለተኛው በቅርቡ ከእስር የተፈታው ወዳጄ አቶ አንዱዓለም አራጌ መስከረም 11/98 በኢዴአፓ መድህን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የተናገረውን ለእሱ በሚፈልገው ሁኔታ ቆርጦ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ያስተላለፉለት ነው፡፡ እዚህ ድረስ መገናኛ ብዙኃንን የተጠቀመ ሰው ዛሬ በወቅቱ አቋማችንን ለማስረዳት ሚዲያ አልነበረንም ሲል መስማት ምን ሊባል እንደሚችል ቸገረኝ፡፡ ጋዜጠኞቹም በበቂ ተዘጋጅተው የሚጠይቁ ባለመሆኑ በየመድረኩ እውነት ትረገጣለች፡፡
3- ወጣት አስጨረስክ የሚሉኝ እኛ ነን እንደውም የታደግነው፤ እኛ እነማን እንደሆኑ የማይታወቅ በመሆኑ እኔ እሱን ብቻ የሚመለከተውን እና የአይን ምስክር የነበርኩበትን ነው የምገልጸው፡፡ ዛሬም ከአስር አመት በኋላ እውነት ተቀብራ የቀረች ይመስል ራስን ነጻ ሌላውን ወንጀለኛ ለማድረግ ከመቸገር የጥፋት ደረጃችን ያንስ ይበዛ እንደሁ እንጂ በዛን ወቅት ከሆነው ማናችንም ነጻ ልንሆን አንችልም፡፡ ስለሆነም በእኔ በኩል ለሆነው ሁሉ የቅርታ እጠይቃለሁ ማለቱ ነበር ሊያስከብር የሚችለው። ይህ ሳይሆን ሲቀርና ዛሬ የተነገረው ትናንት ከሆነው ጋር የማይገናኝ ሲሆን ነገሩን በቅርብ የምናውቅ ሰዎች በስሜት ሳይሆን በእውነት በአሉባልታ ሳሆን በማስረጃ ገልጸን የማሳየት የህሊና ግዴት አለብን፡፡ እናም እነሆ፤
ሀ- የምርጫውን ውጤት ተከትሎ በየፓርቲዎችም በቅንጅትም ውይይት ሲደረግ ምርጫ ቦርድ የመጨረሻውን ውጤት ካሳወቀ በኋላ ካልተስማማን ምን እናደርጋለን ተብሎ እንደ አንድ አማራጭ በቀረበው ፍርድ ቤት መሄድ አለመሄድ ጉዳይ የኢዴፓ ም/ቤት ሲወያይ ልደቱ ያቀረበው ሀሳብ አስደንጋጭም አጠራጣሪም ነበር፡፡ “ምርጫ ቦርድ ውጤቱን ለውጦ ኢህአዴግን አሸናፊ ቢያደርገው ፍርድ ቤት ሄደን የተለየ ነገር ስለማናገኝ የተጭበረበረውን የህዝብ ድምጽ ለማስመለስ ህዝብ ለተቃውሞ እንጠራለን፣ ኢህአዴግ በለመደው መንገድ ይህን የህዝብ ተቃውሞ ሰዎችን በመግደል ያከሽፈዋል፣ ከዚህ በኋላ እኛ ይህንኑ አጋልጠን ያገኘነውን ወንበር ይዘን በፓርላማ ትግላችንን እንቀጥላለን ነበር ያለው፡፡” (ይህን አባባሉን ከውህደት በፊት በነበረውና እኔ አባል ባልነበርኩበት የቅንጅት ምክር ቤትም ማቅረቡን ሰምቻለሁ)፡፡ ሁለቱም ቦታ የነበሩ ሰዎች ከጥቂቶች በስተቀር ዛሬም በህይወት አሉ፡፡
ለ- አኩርፎ ከመቅረቱ በፊት የቅንጅት የህዝብ ግንኙነት ሥልጣንኑ በመጠቀም በአገኘው አጋጣሚ ሁሉ ድምጽህን አስቀምተን አንቀመጥም የኢትዮጵያ ህዝብ ቅንጅት ለሚያደርግልህ ጥሪ ተዘጋጅተህ ጠብቅ ማለቱን በወቅቱ የእለት ሁኔታን ይከታተል የነበረ ሁሉ የሚያውቀው በድምጽም በመስልም ተቀርጾ ያለ ነገር ነው፡፡ ከሌላ ቦታ ቢጠፋ ከኢቲቪ መደርደሪያ ላይ አይጠፋም ይህ አባባል ህብረተሰቡን የሚያረጋጋ ወይንስ የሚያነሳሳ?
መ- በክፍል አንድ ላይ የገለጽኩት መስከረም 29/ምሽት የፓርላማ መግባት አለመግባትን ጉዳይ ከወሰነው የምክር ቤት ስብሰባ በኋላ በተሰጠ መግለጫ ላይ ህዝቡ የመረጠን ፓርላማ ገብተን ወንበር እንድናሞቅ አይደለም በማለት የተናገረውም ቢሆን የሚያረጋጋ ሳይሆን የሚያናጋ ነው፡፡
ሰ-የቃሊቲው የፌዝ ችሎት የአቃቤ ህግ የቪዲዮ ማስረጃዎችን በተመለከተበት ግዜ በስመ አቃቤ ህግነት የቀረበው ሽመልስ ከማል የማስረጃ ጭብጥ ያለውን ሲያሰማ ህገ መንግስታዊውን ሥርዓት በኃይል ለማፍረስ አቅደው ህዝቡን ለዚህ ዓላማቸው ለማነሳሳት ያደረጉትን ቅስቀሳ ያሳይልኛል ይልና ቪዲዮው ሲታይ የተባለውን ሲናገር የሚታየው ልደቱ ነበር፡፡ በዚህ ወቅት ችሎቱን የሚከታተለው ታዳሚ እነ ሽመለስ ከማልን እያየ ያጉረመርማል ግማሹም ፈገግ ይላል፡፡ መሳቅ በችሎት ማወክ ያስቀጣል ተብሎ ማስጠንቀቂያ በመሰጡት እንጂ ብዙዎች ከትከት ብለው ይስቁ እንደነበር ሁኔታቸው ይናገር ነበር፡፡ ከዳኞቹ ፊት ላይ ደግሞ የመገረም ስሜት ሲነበብ አጃቢ ፖለሶች ስክሪን ላይ የሚያዩትን ሰው ከመካከላችን ይፈልጋሉ፡፡ታዲያ ችሎቱ ተነስቶ ስንመለስ እንዴት ነው ነገሩ ቪዲዮው ላይ ያየነው ሰው ከመካከላችሁ የለም አልተከሰሰም ማለት ነው ወዘተ እያሉ ይጠይቁን ነበር፡፡
4- ትናንት ኢህአዴግን ደገፋችሁ ተብለን ተጠላን ዛሬ ሁሉም የኢህአዴግ ደጋፊ ሆነ፤ ይህን ስሰማ ለወዳጄ በእጅጉን አዘንኩለት፤ የት ይደርሳል ብለን በጉጉት ስናየው የነበረ ልጅ መሀል መንገድ ላይ አይሆኑ መሆኑ ሲገርም እንዲህ እስከ ማሰብ መድረሱ የሚያሳዝን ነው፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ከተሳሳትሁ ለመታረም ግጁ ነኝ ህዝቡ የደገፈው ኢህአዴግንም ዶ/ር አብይንም ሳይሆን የታገለለትን የናፈቀውን የተመኘውን የለውጥ ጅማሮ ነው፡፡ ለውጥ ያለ ሰው ስለማይታሰብ ዶ/ር አብይም ሆኑ ቲም ለማ ድጋፍ ያገኙት የለውጡ ተዋናይ በመሆናቸው ነው፡፡ እነርሱ ወደ ሥልጣን መጥተው ለውጥ ባይታይ የሚገጥማቸው ምስጋና ሳይሆን ተቃውሞ እንደነበረ መረዳት ለልደቱ የሚሳን አይመስለኝም፡፡ ነገሩ ወሎዬ ሲያንጎራጉር አላህ ሲቆጣ ብትር አይቆርጥም ያደርጋል እንጂ ነገር እንዳይጥም የሚለው ሆኖ እንጂ፡፡
5- ይቅርታ ጠይቀው ከተፈቱ በኋላ፤ ይህንንም ያነሳው በአዎንታዊ መልኩ አይለም፡፡ ይህ ግልጽ የሚሆነው የመፈረማችን ዜና ከፕ/ር ኤፍሬም ጋር በተስማማንበት መሰረት ሳይሆን መለስ በሚፈልገው መንገድ በመገናኛ ብዙኃን ተነግሮ ገና ሳንፈታ አቶ ልደቱ ተሸቀዳድሞ በመገናኛ ብዙኃን ብቅ በማለት እኛንም ይቅርታ ይጠይቁን ማለቱን ስናስታውስ ነው፡፡ አሁን ግዜ ተለውጧልና ፕ/ር ኤፍሬም ወደ ሞት ከመሄዳቸው በፊት እውነቱን ይናገራሉ ብዬ አስባለሁ፡፡ እባካችሁ ጋዜጠኞችም ጠይቁቸው፡፡ በመጨረሻው ሰአት ላይ ተዋቂው የህግ ባለሙያ አቶ ታምሩ ወንድምአገኘሁም ነበሩበት፡፡
6-የአሉባልታ ፖለቲካ ይሄ እውነት ነው፤ ፕ/ር መረራ የቡዳ ፖለቲካ የሚሉት አደረገው እንጂ፡፡ ለአንድ ዓላማ ተሰልፈው፤ በአንድ ህግ ሊገዙ ቃል ተገባብተው፣ እስከ ሞት አብሮ መዝለቅ የሚጠበቅባቸው የአንድ ፓርቲ ሰዎች የሀሳብ የበላይነት ማግኘት ሲያቅትና በመረጃና ማስረጃ መሞገት ዳገት ሲሆን ቀላሉና አቋራጩ መንገድ አሉባልታ ነው፡፡ይህን የተቃውሞውን ጎራ ድክመት በተለይም በመሪነት ቦታ የሚቀመጡትን ሰዎች ከወንበር በላይ ማሳብ አለመቻል የተረዳው ወያኔ አሉባልታ እየፈበረከ፣ የፍረጃ መርዝ እየቀመመ ይረጫል፡፡ በዚህ ወቅት ወንበሩ ላይ ያሉት ሰከን ብለው ለማጣራት ከመሞከር ይልቅ የማይፈልጉትን ሰው ከአጠገባቸው ለማራቅ በቂ ድጋፍ እንዳገኙ ይቆጥሩትና የበለጠ ያራግቡታል፡፡ ከዛም አባራሪና ተባራሪ ብሎም አዲስ ፓርቲ ይፈጠራል፡፡
የሚገርመው በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በአመራር ቦታ ተቀምጦ አሉባልታና ፍረጃ ያልነካው ቢኖር የታደለ በጣም ጥቂት ሰው ነው፡፡ ዛሬ በሌሎች የተፈረጀ አሉባልታ የተወራበት ሰው ነገ እሱ በተራው ሌሎችን ይፈርጃል አሉባልታ ያስወራል፡፡ ይህ አሌ የማይባል እውነት ሆኖ አጠያያቂውና አስጠያቂው ልደቱ ራሱን ከደሙ ንጹህ አድርጎ ማቅረቡ ነው፡፡ ግዮን ሆቴል አቅራቢያ ከሚገኘውና የእሱ ልዩ ምሽግ ከነበረው(ይህን ያልኩበት ምክንያት አለኝ) ቢሮ እየተፈበረኩ ይወጡ የነበሩ አሉባልታዎችን እየተቀመሙ ይረጩ የነበሩ ፍረጃዎችን አላውቃቸውም እኔን አይመለከቱኝም ይል ይሆን?
የልደቱን ልዩ የሚያደርገው በፊት ለፊትም ሰው ለማጋጨት የሚሰራ መሆኑ ነው፡፡ ማህተም አላደርግም ብሎ እነ ዶ/ር አለማየሁ አረዳ ሽምግልና ተልከው እነርሱም በነገራቸው አምነው ሊያስረዳ በተገኘበት የምክር ቤት ስብሰባ ላይ አላምናችሁም አለ፤ ስለምን ቢባል ከምርጫው በፊት ዶ/ር ብርሀኑና ፕ/ር መስፍን ምርጫው ይለፍ እንጂ ሀይሉን እናነሳልሀለን ብለውኝ ነበር ሲል ተናገረ፡፡ ኢ/ር ኃይሉ ከተሰብሳቢው መሀል ነበሩና ከመቀመጫቸው ብድግ ብለው ወንበሩን ነው የምትፈልገው፤ አትችለውም እንጂ ከቻልከው ዛሬውኑ ውሰደው አሉት፡፡ ያሰበው ነገር አቅጣጫውን ሳተበት፡፡
7-የሚቃወሙን ፖለቲካን ምርጫ 97 የጀመሩ ናቸው፤ ይህን ምን ትሉታላችሁ፤ እኛ የምትለው የወል መጠሪያ መገለጥ ያለባት እዚህ ጋር ነው፡፡በወቅቱ የኢዴአፓ መድህን ም/ቤት ሙሉ ለሙሉ ባይባልም አብዛኛው የእሱ ደጋፊ አልነበረም፡፡የውህዱ ቅንጅት ም/ር ቤት አባል ከነበርነው 18 ሰዎች አስራ ሰባታችን ማህተም አላደርግም በማለቱ ምክንያት ስብሰባ አድርገን በነበረ ግዜ የዘጠኙን ድጋፍ ማግኘት ችሎ ነበር፤ ከላይ በገለጽኩት የምክር ቤት ስብሰባ ላይ ዶ/ር አለማየሁ አረዳ ተነስተው ቃለ ጉባኤ ሰነድ አይደለም ወይ እንዴት አታምነንም፤ በብእር ካለመንህ ጣታችን ቀለም እየነከርን በአሻራችን እንፈርምልህ፤ይህንንም ካላመንህ ጣታችንን እያደማን በደማችን እንፈርምልህ፣ አለ የምትለውን ነገር ሁሉ በአጀንዳ መወያየት እንችላለን ወዘተ ብለውት አሻፈረኝ ሲል ከዘጠኙ ውስጥ የነበሩት ወ/ሮ ላቀች ደገፉ አቶ ጎሹ አውደው( ነብስ ይማር ሁለቱም ሞተዋል) መምህር ወንድ ወሰን ተሾመ (አሁን በዶ/ር ጫኔ በሚመራው ኢዴፓ ውስጥ ናቸው፡፡) በየተራ እየተነሱ ከዚህ በላይ ምን ይፈለጋል ማህተሙን ልታደርግ ይገባል ሲሉት ነበር ከዚህ በላይ አልችልም ብሎ ሹልክ ብሎ ወጥቶ የሄደው፡፡ እንግዲህ እነዚህ ሁሉ ፖለቲካን በምርጫ 97 የጀመሩ ናቸው ማለት ነው፡፡ ያሳዝናል አሁንም ጥሩ መካሪ ያገኘ አይመስለኝም፡፡በየቦታው የመናገር ምቹ ሁኔታ ማግኘቱን ዳግም እንደማንሰራራት ቆጥሮት ከሆነ ንግግሩ ሲበዛ ስህተቱ ይጨምራል የሚለውን አባባል ማስታወሱ ሳይበጅ አይቀርም፡፡
“መከበርና መዋረድህ ከቃልህ የተነሳ ነው፤ የሰው መከራው በአንደበቱ ከተናገረው የተነሳ ነው፡፡” መጽኃፈ ሲራክ 5/14 ይጠቅም ከሆነ አንድ ዓላማዊ አባባልም ላክል፡፡ “በዚህ ዓለም ማንም ሰው ለውድቀት የሚያበቃ ዕቅድ የሚያወጣ የለም፤ ትክክለኛ ዕቅድ ባለማውጣታቸው ግን እነዚህ የተባሉት ይሆናሉ፤ ትክክለኛ ዕቅድ አለማውጣት ራስን ለውድቀት ማዘጋጀት

Friday, August 9, 2019


The basic skills of facilitator
====================


we often experience moods of anger & joy .we do have remarkable ability to learn and memorize events .We often notice powerful effect of leaders on behaviour of followers .
While we interact in groups we often experience conflict and cooperation.
At times we suffer from depression hyper anxiety . All of us remain curious to know about the causes of these happenings and try to make sense in own ways .
The knowledge gathered in this way cannot be used to formulate theories or to solve problems faced by peoples in their lives . We need dependable and relatively & accurate understanding the principles of describing the working human mind and behaviour.
The basic skills of facilitator following good meeting practices , timekeeping and minimizing self bias
Accuracy and Bias in self Perception
--------------------------------------------------------------
Self insight or accuracy of self perception, has been an issue of longstanding concerns to philosophers and social scientists . Among contemporary psychologists ,two different points of view predominant . According to one view, perception of self are based on socially shared reality ensue from the same processes the perception of others are best thought as accurate of behaviour and experience.
According to others view self perception is fundamentally distorted, self serving , and more consistent by self serving, and more positive than is justified by the perception of others .
Some psychologists discuss illusory self-enhancement if it were general law of human behaviour applicable to all normal psychologically healthy individual
Normal human thought is marked not by accuracy but by positive self enhancing illusions "the healthy person is prone to self deceptive s positively"
The team-building Overview
--------------------------------------------------------
Team building activities exercises that help teams building cohesion and work through common group issues and provide opportunities for participants to combine individual talents and abilities with awareness of the need to develop cooperation and trust within a group.
As people interact, they form relationship based on their own motivations and understanding of the other parties intentions & desires. Similarly people who represent an organization, political party or a group of people must bridge relationship when interacting with others. The corner stone of creating a constructive and working relationship among people whether they are representatives of something greater or not , is understanding that all parties involved have desire outcome . In most cases the desired outcomes of or motives of the other involved parties . With the later in mind ,individuals can improve their chance of successful working relationships if they understand where they themselves are coming from and where they are going.

Monday, January 7, 2019

"በአንድ ሀገር ውስጥ እስከ አፍንጫቸው የታጠቁ ክልሎች ሊኖሩ አይገባም" ፕሮፌ. ብርሃኑ


Sunday, January 6, 2019

ያልተገራው የማንነት ፖለቲካችን እና አደጋው (ተበጀ ሞላ (PhD)


The Poison of Ethnic Federalism in Ethiopia’s Body Politic
መግቢያ
በሀገራችን የዘውጌ ፖለቲካ ያለ ልክ ጦዟል።  በየማዕዘኑ ዘውጌ-ተኮር አፍራሽ ፉከራ እና ዲስኩር እየሰማን ነው። ፖለቲካኞቻችንም ሃሳብ ከመሸጥ ይልቅ ስሜት መግዛት ላይ አትኩረዋል።  በግዜ እልባት ካላገኘ ይሄ አካሄድ ሀገር አልባ እንዳያስቀረን ያስጋል። ለመሆኑ የዘውጌ ፖለቲካ ታሪካዊ መሰረቱ ምንድነው? ከኛ ተጨባጭ ሁኔታ አንፃርስ አክራሪ ዘውጌነት ምን አደጋ አለው? አሳታፊ የሆነ የዜግነት ፖለቲካ እዉን እንዲሆን ምን የተሻለ መንገድ አለ? ይህ አጭር መጣጥፍ እነዚህን ነጥቦች በጨረፍታ ይዳስሳል። በፅሁፉ ዉስጥ ዘውጌ፣ ዘውግ እና ብሔር የሚሉት ቃላት እንደ ቅደም ተከተላቸው ethnic፣ ethnicity እና nation የሚሉትን የእንግሊዝኛ ቃላት ይተካሉ።  ሃሳቤን ማንነትን በማብራራት እጀምራለሁ።
ማንነት ምንድን ነው?
ማንነት ከሌሎች ጋር ባለን ግንኙነት በቡድንም ሆነ በግለሰብ ደረጃ ራሳችንን የምንገልፅበት መለያችን ነው። በዋናነት ማንነት ለራስ በሚሰጥ እይታ ይገለፃል። ማንነት ዘርፈ-ብዙ ነው።  ነጠላ ማንነት ያለው ሰው የለም። አንድ ግለሰብ በፆታው፣ በሃይማኖቱ፣ በቋንቋው፣ በዘውጉ፣ በሙያዉ፣ በፖለቲካ እምነቱ እና አሰላለፉ፣ ወዘተ ማንነቱን ሊገልፅ ይችላል። ከሁለንተናዊው ሰውነቷ ባሻገር ሶፊያ  ባንድ ግዜ ሙስሊም ፣ መምህር፣ ስልጤ፣ ኢትዮጵያዊት፣ የአፍሪካ ሴት ልትሆን ትችላለች። በመሆኑም ‘ይህ ቡድን ወይም ያ ግለሰብ የተለየ ማንነት አለው’ ሲባል የግድ ስለ ዘዉግ አያወራን ላይሆን ይችላል። በሌላ አነጋገር ማንነት እንደ ቀይ ሽንኩርት ተደራራቢ ነው። አንዱን ንብር ልጦ ጥሎ (ረስቶ) ሌላውን መብላት (ማስጮህ) የባለቤቱ ምርጫ ነው።
ሰው ነን እና ኑሯችን ከሌሎች ጋር የተቆራኘ ነው። ስዉር በሆነው የግል ማንነታችን እና ሁለንተናዊ (universal) በሆነው ሰዋዊ ተፈጥሯችን መካከል ራሳችንን በበርካታ የጋርዮሽ እርከን እናገኘዋለን። ከቤተሰብ ጀምረን ከፍ ስንል በዘመድ አዝማድ ከዛም ሲያልፍ በጎሳ (clan)፣ በዘውግ (ethnicity)፣ በነገድ (tribe)፣ በብሔር (nation) እና በዘር (race) ማንነታችንን እንገልፃለን። አንደ አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ ደግሞ የዉጭ ሰዎች በብሔራዊ ማንነታችንን (national identity) ይለዩናል።
በሊብራል ዲሞክራቲክ ሃገራት እንደ አዲስ ያቆጠቆጠውን አክራሪ ብሄርተኝነት ተከትሎ ስለ ማንነት ፖለቲካ ብዙ ትንታኔ አየተሰጠ ነው። እዉቁ የፖለቲካ ሳይንስ ተመራማሪ ፍራንሲስ ፍኩያማ እና አፍሪቃዊው ፈላስፋ ክዋሜ አፕያህ በቅርቡ በማንነት ላይ ያሳተሟቸው መፅሃፍት ተጠቃሽ ናቸው።  እንደ ፍኩያማ እምነት የሰው ልጅ ለእዉቅና (recognition) የተለየ ቦታ አለው። ለማንነት የሚሰጥ እዉቅና ከክብር ጋር ይያያዛል። ማንነቴ ተገቢዉን እዉቅና ዋጋ አላገኘም ብሎ ያመነ ግለሰብም ሆነ ቡድን ይደራጃል፣ ይታገላል። አፕያህ በበኩሉ ማንነት እንደ ዘረመል (gene) የሚወረስ ሳይሆን እንደ ፀጉር በቅጥ ተሰርቶ ማድመቂያ የሚሆን ስሪት ነው ሲል ይከራከራል ። የዘውጌ ማንነት በዋናነት ተወራሽ መለያወችን (primordial characteristics) መሰረት ያደረገ ነው። አባላቱ ‘እኛና እነሱ’ ብለው የሚለዩባቸው ቋንቋ ፣ ወግና ልማድ እንዲሁም ግዛት (ancestral territory) ይጋራሉ። ሆኖም ማንነት ተፈጥሯዊ አይደለም — ሰው ሰራሽ ነው።  አዲስ ግዛት በመዉረር፣ ባህልን በማሻሻል እና ታሪክን ለራስ በሚመች መልኩ በመከለስ የዘውጌ ማንነት ይፈጠራል። ለዚህ ደግሞ የፖለቲካ ኃይል፣ ትውፊት እና ዲስኩር ዋና መሳሪያዎች ናቸው።  ካለፉት 30 አመታት ጀምሮ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ምሕዳር እየሆነ ያለዉን ያስተዋለ ይህን እዉነታ  አይስተውም።
የብሔር ፖለቲካ አመጣጥ በጨረፍታ 
ብሔር እና የብሔር ፖለቲካ መነሻ አዉሮፓ ነው። በዘርፉ ጥልቅ ምርምር ያደረገው ሊህ ግርንፈልድ እንደሚለው nation (ብሔር) የሚለው ፅንሰ-ሃሳብ ምንጩ natio የሚለው የላቲን ቃል ሲሆን ትርጉሙም ‘የተወለደ’ ማለት ነው። የጥንት ሮማዉያን ቃሉን ካንድ አካባቢ የመጡ የዉጭ ሃገር  ሰዎችን ለመግለፅ ይጠቀሙበት እንደነበር ተዘግቧል። በዋናነት መጤነትን ስለሚገልፅ ትርጓሜው የክብረነክነት ባህሪ ነበረው። ሁላ በመካከለኛው የአዉሮጳዉያን ታሪክ ብሔር የሚለው ስያሜ በቋንቋ ወይም በትዉልድ ቦታ  ከሚመሳሰሉ አካባቢዎች የመጡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ለመግለፅ ይዉል ነበር ። ተማሪዎቹም የትዉልድ ቄያቸውን መሰረት አድርገው መተጋገዝ እና በክርክርም ወቅት አንድ ላይ መቆም መለያቸው ስለነበር ብሔር የሚለው ስያሜ ያንድ አካባቢ ሰዎችን ብቻ ሳይሆን ሃሳብ እና ዓላማ ለሚጋሩ ማህበረሰቦች (communities) መጠሪያ ሊሆን በቃ።  ቆይቶም ሃሳቡ ወደ ቤተክህነት ጉባኤ ዘልቆ ገባ እና ሌላ ትርጉሙ አገኘ: ልሂቃንን ለመግለፅ ዋለ። በ16ኛው ዘመን እንግሊዞች  ብሔርን እና   ‘ሕዝብ’ን በእብረታ (አንድ ላይ) መጠቀም እንደጀመሩ  ይነገራል። ይህ ለውጥ ሃገራዊ ብሄርተኝነት (civic nationalism) የፖለቲካ ርዕዮተ-ዓለም እንዲሆን ርሾ የጣለ ነበር።
ከ18ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ግን ብሔር የሚለው ቃል ‘ልዩ ሕዝብ’ የሚል ትርጉም ያዘ። በፈረንሳይ፣ ጀርመን እና ሩስያ ቃሉ ዘውግን፣ ግዛትን እና የፖለቲካ ታማኝነትን አጣምሮ የያዘ ማህበረሰብ የሚገልፅ ሆነ።  በተለይ ደግሞ በፈረንሳይ አብዮት ማግስት የተቀነቀነው ‘የብሔር ጥያቄ’ ከ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ  ጀምሮ በግራ-ዘመም ፖለቲከኞች ቁልፍ አጀንዳ ለመሆን በቅቷል።  ብሔር እና ብሔረሰብን ዋና የፖለቲካ ጉዳይ  አድርጎ ለመጀመርያ ያቀረበው የሶቪየቱ መሪ ጆሴፍ ስታሊን ማርክሲዝም እና የብሔር ጥያቄ በሚለው ፅሁፉ (1913 እአአ) ብሔር መሰረቱ የግድ ዘር፣ ነገድ ወይም ዘውግ ላይሆን ይችላል ይላል። በዋንናነት የኦቶ ባወርን (በወቅቱ ስመ-ጥር የነበረ ኦስትርያዊ ፖለቲከኛ) ሥራ መሰረት አድርጎ፣ ስታሊን   ብሔር ማለት ታሪካዊ ሂደት፣ ቋንቋ፣  አሰፋፈርና ስነ-ልቦና የሚጋራ እና የምጣኔ ሀብት ትሥሥር ያለው ማህበረሰብ ነው ሲል አብራርቷል።
በዚህ መልኩ ቅርፅ የያዘው የብሔር ፖለቲካ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማግስት ጀምሮ  ከአዉሮጳ ወደ ሌሎች ክፍለ-ዓለማት በሰፊው ተዛመተ። የአፍሪካ ልሂቃን በሌላ አዉድ ስለ ብሔር የተፃፈውን እና የተነገረውን ሁሉ ገልብጠው ለዘውግ ፖለቲካ አዋሉት።  የኛዎቹ ዋለልኝ መኮንን እና መለስ ዜናዊም ይህንኑ ነበር ያደረጉት። ሃሳቡን ሲዋሱ አግባበ ነገሩን ግን አላገናዘቡም። ከላይ እንደተባለው ብሔር (nation) የሚለው ቃል በታሪክ ሂደት ብዙ ግዜ ትርጉሙ ተለዉጧል፥ ለሮማዉያን የመጤ ሰዎች መጠሪያ ነበር። ቆይቶ  ሃሳብ እና ዓላማ የሚጋሩ ስብስቦችን ለመግለፅ ዋለ።  ኋላ ደግሞ የሃይማኖት እና ማህበራዊ ልሂቃን ስያሜ ተደረገ። ከዛም እንግሊዞች ‘ሉዓላዊ  ሕዝብ’ የሚለውን ፖለቲካዊ ትርጉም አስያዙት። በዘመነ አብዮት ደግሞ ብሔር ማለት ‘ልዩ ሕዝብ’ ማለት ሆነ። የ ‘ያ ትውልድ’ ዘውጌዎች እና የዛሬዎቹ ደቀመዝሙሮቻቸው ‘ብሔር’ ነን ሲሉ “ሌሎች ጋር ምንም የማንጋራ ‘ልዩ’ ሕዝብ ነን” ማለታቸው ነው። ኢትዮጵያን በቅጡ ለሚያውቅ እሳቤው የተዛባ ነው። ከሀገራዊ ብሔርተኝነት (civic nationalism) እደገት እና ታሪክ አንፃር ሲታይ ብሔር ማለት እጣ ፈንታው አንድ የሆነ፣ ከሚያለያዩት የዘውጌና ሌሎች ማንነቶች ባለፈ ጠንካራ የጋራ እሴቶች ያሉት ሕዝብ ማለት ነው። ስለዚህ ፖለቲካችን በብሔር ደረጃ ከሆነ የምናወራው ስለ አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንጂ ስለ ዘውጌ ማንነት ሊሆን አይችልም።
የኢትዮጵያ ብሔር እና ብሔረሰብ እነማን ናቸው?
እንደማንኛውም መድብለ-ዘውጌ ማህበረሰብ (multi-ethnic society) በኢትዮጵያ ከዘዉዳዊዉ ስርዓት ግርሰሳ ጀምሮ፣ በተለይ ደግሞ ኢሕአዴግ ወደ ስልጣን ከወጣ ወዲህ ‘የብሔር ጥያቄ’ ዋና የፖለቲካ ጉዳይ ሆኖ ቆይቷል። የሶቭየትን (1936/1977 እአአ) እና ዩጎስላቪያን (1946/1974 እአአ) ህገ-መንግስቶች ፈለግ ተከትሎ ወታደራዊው ስርዓት በሕገ-መንግስቱ (አንቅፅ 2) ኢትዮጵያ የብሔረሰቦች ሀገር መሆኗን አስቀምጦ ነበር። በተመሳሳይ አራተኛው (አሁን በሥራ ላይ ያለው) ህገ-መንግስት በሀገሪቱ  ሉዓላዊ  የሰልጣን ባለቤቶች  ‘ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች’ ናቸው ይላል። ነገር ግን በሕገ-መንግስቱ የሰፈሩት አንዳንዶቹ  የፖለቲካ ቃላት አስማሚ እና ግልፅ ብያኔ የላቸውም። ለምሳሌ ስታሊን ለብሔር የሰጠውን ብያኔ የኢትዮጵያ ህገ-መንግስት ‘ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦችን’ የሚለውን ፈርጅ (category) ለመግለጽ ተጠቅሞበታል። አንቅፅ 39(5) ‘ብሔር፣ ብሔረሰብ፣ ሕዝብ’ ማለት “ሰፋ ያለ የጋራ ጠባይ የማንፀባርቅ ባህል ወይም ተመሳሳይ ልምዶች ያላቸው፣ ሊግባቡበት የሚችሉበት የጋራ ቋንቋ ያላቸው፣የጋራ ወይም የተዛመደ ሕልዉና አለን ብለው የሚያምኑ፣ የስነ-ልቦና አንድነት ያላቸውና በአብዛኛው በተያያዘ መልክዓምድር የሚኖሩ ናቸው” ብሎ ይፈታዋል።  ፅንሰ-ሃሳቡ በቀጥታ ከስታሊን ፍች አለያም ከመሰል ምንጭ የተቀዳ በመሆኑ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ማን ብሔር፣ ማን ብሔረሰብ፣ ማን ሕዝብ እንደሆነ በግልፅ አልተቀመጠም። በ1984 ብሔራዊ ክልላዊ መስተዳድሮችን ለማቋቋም የወጣው አዋጅ (ቁጥር 7/1984) ደግሞ ብሔርና ብሔረሰብ ተተካኪ እንደሆኑ አድርጎ አስቀምቷቸዋል። አንቅፅ 2(7) “‘ብሔር’ ወይም ‘ብሔረሰብ’ ማለት በአንድ ኩታ ገጠም መልክዓ ምድር የሚኖር አንድ የመግባብያ ቋንቋና የአንድነት ስነልቦና ያለው ሕዝብ ነው” ይላል። በተመሳስይ መልኩ የሚድያ ባለሙያዎች እና ፖለቲከኞች ብሔርና ብሔረሰብ የሚሉትን ቃላት የዘውጌ ቡድኖችን (ethnic groups) ለመግለፅ ይጠቀሙበታል።
የዘውጌ ማንነትን የተረዳንበት እና ፖለቲካዊ ጥያቄውን ምላሽ ለመስጠት የሄድንበት መንገድ ከሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ጋር ያልተዛመደ በመሆኑ አሁን ላለንበት ችግር ደርሰናል። የክልል መንግስታት ምስረታና ስያሜ ጥሩ ማሳያ ነው ። ከላይ በተጠቀሰው አዋጅ መሰረት በትግራይ ክልል ትግራዋይ፣ ኩናማና ሳሆ የሚባሉ የዘውጌ ቡድኖች ይኖራሉ። በደቡብ ትግራይ ያሉ ራያዎችም አማርኛ፣ ኦሮምኛና አገዉኛ ይናገራሉ። በአማራ ክልልም እንዲሁ የአማራ፣ አገው፣ ኦሮሞ፣ አርጎባ እና ሌሎች ማሕበረሰቦች ይኖራሉ። ኦሮምያም በዉስጡ በርካታ የዘውጌ ማንነት ያላቸው ህዝቦች ይዟል።  የጋምቤላ እና  የቤንሻንጉል  ጉሙዝ ክልሎችም  የተለያዩ የዘውጌ ቡድኖች መኖርያ ናቸው።  ነገር ግን የክልላዊ መንግሥታት ስያሜ እና ክለላ ይህን የብዝሃነት እዉነታ አያንፀባርቅም። የትግራይን ክልላዊ መንግስት  “ብሔራዊ ”  በሚል  ከፍታ አስቀምጦ  ጋምቤላን “የብሔረሰቦችእና ህዝቦች  ክልል ብሎ መሰየም  የምስቅልቅሉ ሁነኛ ማሳያ ነው።  ከፊት ለፊት ሲታይ ችግሩ  የፅንሰ-ሃሳብ ግልፅነት (conceptual clarity) ሳይኖር ህገ-መንግስቱ በመተርጎሙ የመጣ ይመስላል። ሸፍጥ የለበትም ብሎ መደምደም ግን አይቻልም።
በንድፈ-ሃሳብ ደረጃ ዊል ኪምሊካ የተባለ የዘርፉ ተመራማሪ በመድብለ-ዘውጌ ማህበረሰብ  ዉስጥ በቁጥር እና ንቃተ-ህሊና ከፍ ያሉ የዘውጌ ቡድኖች ብሔር ሲባሉ ቀሪዎቹ ብሔረሰብ (nationality) ተብለው ሊሰየሙ ይቻላል ይላል። ነገር ግን ፍረጃው ሳይንሳዊ አይደልም፣ አያሳምንም። አንድ ዘውግ አናሳ የሚባለው መቼ ነው? ሰያሚውስ ማነው? ፖለቲካዊ ንቃተ-ሕሊናስ በምን ይለካል? ኢትይጵያ ዉስጥ ኦሮሞ እና አማራን ብሔር፣ ጋሞ እና ስልጤን ደግሞ ብሔረሰብ ብሎ ለመለየት አሳማኝ ቀመር የለም።
 አክራሪው የዘውጌ  ፖለቲካችን  የሳታቸው አምስት ቁምነገሮች 
በሰው ልጅ ታሪክ ለረጅም ግዜ ፖለቲካዊ ቅቡልነት (legitimacy) ምንጩ እግዚአብሔር ወይም ስርወ-መንግስት ነበር። ባንዳንድ የዓለማችን ክፍሎች አሁንም የስልጣን ምንጭ ደም ወይም ፈጣሪ ቢሆንም በአብዘሀኛው ዘመናዊ ፖለቲካ መሰረቱ በማንነት ዙሪያ የተሰባሰበ ሕዝብ ነው። የሙያ ማህበራት፣ የሃይማኖት ተቋማት፣ ጥቁሮች ፣ ወግ አጥባቂዎች ወዘተ በፖለቲካው ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩት በማንነት ስም በሚሰበስቡት ድምፅ ነው። በኢትዮጵያም የስልጣን ምንጭ እግዜር ነበር። ቆይቶ ርዕዮተ-ዓለም ሆነ። አሁን የሁሉም ነገር ምንጩ ዘውግ ሆኗል። መጀምርያ የስታሊንን የብሔር ፖለቲካ የሸመደዱ የ1960ቹ ተማሪዎች የዘውዱን ስርዓት በብሔር እና መደብ ጭቆና ስም ታገሉት።  የመደብ ጭቆናው በወታደራዊ መንግስት ሲመለስ ዘውጌዎቹ የብሔር ጥያቄ አንጠልጥለው በረሃ ገቡ፣ አሸነፉበትም። አሸናፊዎቹ በተራቸው ፍላጎታቸውን በሌሎቻችን ላይ ጫኑ። ተጨቋኞቹ ሌላ ዙር ትግል አድርገው ዛሬ ላይ ደርሰናል። አሁንም የፖለቲካ ችግራችን እንደተወሳሰበ ነው።  በኔ እይታ ያልተገራ እና መሬት ያልያዘ  የዘውጌ ፖለቲካ ለችግራችን ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል። አምስት መከራከርያ ነጥቦችን ላንሳ።
አንደኛ ማንነት ሰው ሰራሽ እንደመሆኑ ቋሚ አይደልም። የታሪካዊ ግስጋሴ (historical progress)  በህዝቦች ዉህደት እና የባህል ዉርስ ይገለፃል። ለምሳሌ ብሔር የአዝጋሚ እድገት (evolution)  ዉጤት ነው። ለረጅም ጊዜ በሚዘልቅ  ጥልቅ የህዝቦች መስተጋብር ምክንያት ቤተሰብ ወደ ጎሳ፣ ጎሳም ወደ ዘዉግ፣ ዘዉግም ወደ ብሔር ያድጋል። ቁሳዊ ልማት እና የባህል ሽግግርም እንዲሁ ወሳኝ ነው። በነዲክት አንደርሰን ‘ብሔር ምናባዊ ማሕበረሰብ’ ነው ሲል ስሪትነቱን ለመጠቆም ነው።  ዛሬ ጥቁር፣ ነጭ፣ ምስራቃዊ (oriental) ወዘተ የምንላቸው የሰው ዘር ፈርጆች እንኳ ከሁለት ሚሊንየም በፊት አልበሩም። በምዕራብ አዉሮፓም ጎሳ፣ ዘውግ እና ነገድ  ታሪካዊ ሂደቱን ተከትሎ ወደ ብሔር አድጓል ።  ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ እና ጣልያን የመሳሰሉት ሃገራት የግዛት ወሰናቸውን ከብሔር ክልል ጋር በማጣጣም ወጥ መንግስታዊ  አስተዳደር ወይም ብሔረ-መንግስት (nation-state) መስርተዋል።  የፈረንሳይ ብሔር ጉዓል፣ ሮማን፣ ብርቶን፣ ተኦቶን የመሳሰሉ ነገዶችን እና ጎሳዎችን በሂደት አዋህዶ የተፈጠረ ነው። የጣልያን ብሄርም እንዲሁ ሮማን፣ ኢትራስካን፣ ተኦቶን፣ ግሪክ እና አረብ ዘር ያላቸውን ህዝቦች ያዋሐደ ነው። በሌላ በኩል የህዝቦች መስተጋብር ዉስን በሆነባቸው፣ ለረጅም ግዜ ጎልቶ የወጣ ጠንካራ የፖለቲካ ማሕበረሰብ ባልተፈጠረባቸው እና በቁሳዊ ልማት ወደ ሁላ በቀሩ የኤሽያ እና የአፍሪካ ሃገራት ዉስጥ ለቁጥር የሚያታክቱ ጎሳዎች እና ዘውጌ ማህበረሰቦች መኖራቸው ማኅበረሰባዊ አዝጋሚ ለዉጥ ከቦታ ቦታ እንደሚለያይ ይጠቁማል። ለምሳሌ በኢንዶነዢያ ከ700 የሚበልጡ እንዲሁም በናይጄሪያ ከ500 የሚልቁ የዘውጌ ቡድኖች ይገኛሉ። የነዚህ ህዝቦች መስተጋብር ፍጥነት እና ዉጤት የሚወስነው በትምሀርት፣ በባህል ና በፖለቲካው ዘርፍ  በሚሰሩ የጋራ እሴት ግንባታ ስራዎች ይሆናል። የሀገራችንም ዕጣ ፈንታ ከዚህ የተለየ አይደለም።
ሁለተኛ ለአክራሪ ዘውጌዎች የመገንጠል መብት (አንቅፅ 39)  ህገ-መንግስታዊ ዋስትና ነው፣ ግዜውን ጠብቆ እንደሚበትንነን አልታያቸውም፣ አልያም ብንበተን ግድ አይላቸውም። ጎርፍ ሲወስድ እያሳሳቀ ነው እንዲሉ፣ ከኛ ቀድመው በሃሳቡ ላይ ሙክረት (experiment) ያደረጉ ከስህተታቸው ለመማር እንኳ ዕድል ሳያገኙ ጠፍተዋል። ፕሬዚደንት ጆሲፕ ቲቶ በ1974 (እአአ) የብሔሮች እና ብሔረሰቦች የመገንጠል መብት በሕገ-መንግስት እንዲረጋገጥ ሲያደርግ ሃገሩ ዩጎዝላቪያ ከ17 ዓመታት ቡሁላ እንደምትበተን አልተረጠረም። የሶቭየት መሪዎችም በ1977 (እአአ) ባሻሻሉት ህገ-መንግስት የህብረቱ አባላት ባሻቸው ግዜ የመገንጠል መብት እንዳላቸው ሲዉጁ ከ14 ዓመታት ቡሁላ ግዛታቸው ከ15 ቦታ እንደሚፈረካከስ አልታያቸውም። ሃሳቡ እነሱን እንዳጠፋቸው እያወቅን ራሳችንን ለማዳን ሌላ አማራጭ መንገድ አለመከተላችን ግራ ያጋባል (የኛ ህገ-መንግስት ሲጸድቅ ከዩጎዝላቪያ እና ሶቭየት ህብረት ፍርስራሽ አዳዲስ ሃገራት እየተመሰረቱ እንደነበር ልብ ይሏል)። ሌላው አስገራሚው እና ከንካኙ ነገር ደግሞ ከ80 በላይ የዘውጌ  ቡድኖች በሚኖሩባት ሀገር የመገንጠል ሀገ-መንግስታዊ መብት  የተረቀቀው ሁለት ቡድኖች ብቻ በሚወክሉት ህወሓት እና ኦነግ ነበር። ብዙሃኑ ድምፅ አልበረውም። ዳግም ዕድል ሊሰጠው ይገባል። በኢትዮጵያ ጉዳይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ድርሻ እንዳለው በተግባር መገለፅ አለበት።
ሶስተኛ አክራሪ የዘውጌ ፖለቲካ ለዉህድ፣ ንዑስ እና ተደራቢ ማንነት ቦታ የለውም፤ ትኩረቱ ነጠላ፣ ጠባብ እና ‘ንፁህ’ ማንነት ላይ ነው። ከዘውግ ባሻግር ሕልዉና ያላቸውን እንደ አዲስ አበባዉያን ያሉ ኮስሞፖሊታን ማህበረሰቦች እና የተውልድ ሃረጋቸውን ከተለያዩ የዘውጌ ቡድኖች የሚስቡ ግለሰቦችን ፍላጎትና ምርጫ አያስተናግድም።  አንድ ተጨባጭ ምሳሌ ላንሳ፣ በሰሜን ምስራቅ ኢትዮጵያ የሚኖር ራያ የሚባል ማህበረሰብ አለ። በታሪክ አጋጣሚ በትግራይ እና አማራ ክልሎች ለሁለት ተከፍሎ ይኖራል። በቅርቡ የራያን ሕዝብ ወደ አንድ አስተዳደራዊ መዋቅር ለማምጣት የተጀመረውን እንቅስቃሴ ተከትሎ ሁለት ኃይሎች ፅንፍ ይዘው ቆመዋል። ህወሓት “ራያ የሚባል ማንነት የለም፣ ራያ ትግሬ ነው” ሲል፣ አብን (አማራ ብሔራዊ ንቅናቄ) ደግሞ “ራያ የሚባል ማንነት የለም፤ ራያ አማራ ነው” ብሎ ሌላ ጫፍ ይዟል። የራያን ኦሮሞነትም የበለጠ ለማጉላት የሚጥሩ የዘዉጌ ፖለቲከኞች አሉ። እዉነታው ግን ራያ ከአማራ፣ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ አፋር እና አገው የሚወለድ ሕብራዊ ዉህድ ማንነት ያለው ሕዝብ ነው። ከማህበረሰቡ  ባህላዊና ታሪካዊ መስተጋብር አንፃር ለራያ የሚስማማው ዜግነትን መሰረት ያደርገ ብሄርተኝነት ነው። የማንነት ሁሉ መለክያ የግድ ዘውግ ብቻ መሆን ስለሌለበት የራያ ሕዝብ ከኢትዮጵያዊነት ባነሰ ማንነት ራሱን ይግለፅ ከተባለ ራያ እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም። ከዚህ ዉጭ በአንድ ዘውግ ወይም ‘ብሔር’ ስም ይጠራ  ቢባል የዘውግ ሃረጋቸውን  ከሌላ አቅጣጫ የሚስቡ የማህበረስቡን ክፍሎች ማግለል ይሆናል።  የዚህ ክትለት (implication) ግልፅ ነው፡ ራያን የመሰሉ ዉህድ ኢትዮጵያዉያን በማንነት ፖለቲካ ባግባቡ አይስተናገዱም፣ ይጠባቸዋል።
አራተኛ አክራሪ የዘውጌ ፖለቲካ ሃገራዊ ብሔርተኝነትን እንደመዳረሻ አያይም። ይባስ ብሎም የትግል ኢላማው ለአንድነት በሚሰሩ የፖለቲካ ኃይሎች ላይ ያነጣጠረ ነው። የኦሮሞ፣ የትግራይ እና የአማራ ዘውጌዎች  ኢትዮጵያዊነትን ማዕከል አድርገው በተነሱ የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ የሚያደርጉት አፍርሽ ቅስቀሳ የዚሁ ችግር ማሳያ ነው። በመሰረቱ ሃገራዊ ብሄርተኝነት እና የዘውጌ (ethnic) ማንነት አይቃረኑም። በብልሃት ከተያዙ ተመጋጋቢ ሆነው መኖር ይችላሉ። ዮሩባው ናይጄሪያዊነቱን፣ ፑንጃቢው ህንዳዊነቱን እንዳልጣለ ሁሉ ኦሮሞውም ሆነ አማራው ኢትዮጵያዊነቱን እና ንዑስ ማንነቱን አስማምቶ  መኖር ይቻለዋል። መሬት ላይ ያለው እውነታም ይህንኑ እንድናደርግ ያስገድደናል። ከፖለቲካው ዲስኩር ባሻገር፣ በተግባር ሀልዉናችን የተሳሰረ ነው።
በመጨረሻም የማንነት ፖለቲካ ‘የኔ’ ከሚለው ቡድን ያልተገደበ እሽታ ይጠብቃል። ልዩነትንና   የሃሳብ ፍጭትን አያስተናግድም። ይህ አጉል ተስፋ ከሰዋዊና ማህበረሰባዊ ተፈጥሯችን ጋር አይገጥምም።  የሰው ልጅ ከራሱ ጋር እንኳ  ፍፁም አንድነት መፍጠር አይችልም። የ10 ደቂቃ ጥሞና  (meditation) ለማድረግ የተቀመጠን ይህን እዉነታ በተግባር እናውቀዋለን። እንደ ነፋስ የሚበተነውን ሃሳባችንን ሰብስበን ማቆም ፈታኝ ነው። ይህ እንግዲህ ከራስ ጋር ለመግባባት የሚደረግ ትግል ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ፣ ጃቆስ ላካን the mirror stage በሚለው የሰውን ልጅ እድገት  ባብራራበት ንደፈ ሐሳቡ ዉስጣዊ ስሜት እና ዉጫዊ ስሌት ብዙውን ግዜ አይጣጣሙም፣ እንዲያ ሲሆን ጭንቀት ይፈጥራል ይላል። ለምሳሌ ዘውጌ-ተኮር የፖለቲካ እንቅስቃሴ ግለሰቡ ራሱን የሚያይበት ማህበራዊ መስታዉት ነው። እንደ አባል ተስፋውን እና ምኞቱን ይገልፅበታል፣ ያነብበታል። እንደግለሰብ ደግሞ መስታዉቱ የማያሳይለት ዉስጣዊ ፍላጎት እና ትግል ይኖረዋል። የዉስጡን እና የዉጩን  ሙሉ ለሙሉ  ማገጣጠም የሚቻል አይደለም።  ፖለቲካዊ አንድምታው በግለሰብም ሆነ በቡድን ደረጃ ከሌሎች ፍፁም አንድነትን መጠበቅ እንደሌለብን ነው። ዘውጌዎች ይህን እዉነታ አይቀበሉም። የነሱን ቋንቋ የሚናገር ሁሉ እንደነሱ እንዲያስብ፣ እንዲሰማው እና እንዲያደር ይጠብቃሉ።
ከዚህ ወዴት
ዘግይቶም ቢሆን ኢህአዴግ ሃገራዊ ማንነትን ችላ ማለት የሚያስከትለው አደጋ ተገልጦለት ነበር። በስልጣን ላይ የነበሩት ኃይሎች ከሁለት ዓመት በፊት አዲስ ራዕይ በምትባል የንድፈ-ሃሳብ መፅሄታቸው በኢትዮጵያዊነት ተኮትኩቶ ያላደገ ወጣት የዘውጌ ወጀብ ቀስቅሶ ሊያጠፋቸው አንደደረሰ ተናዘዋል። የፈሩት አልቀረም፣ ድምፅ አልባው አብዮት ገፍቶ ዳር ጥሏቸዋል። ዉጤቱም ተስፋና ስጋት ወልዷል። በደቡብ ማቆምያ የሌለው የክልልነት ጥያቄ፣ በሰሜን የምናየው እልህና ፍጥጫ፣ በምስራቅ በኩል ሕይወት የቀጠፈው የወሰን ግፍያ፣ በምዕራብ የሚርመሰመሰው ደም አፍሳሽ አማጺ፣ በመሃል የሚራገበው ፅንፈኛ ዘውጌነት ወዘተ ከለት ወደለት የለውጥ ተስፋችን በስጋት እንዲደበዝዝ አድርጎታል። በግዜ ካተገራ በየአቅጣጫው የጦዘው ግለኝነት ሃገር ሊያፈርስ ይችላል።
ከዚህ ስጋት በመነሳት  ይጠቅሙ ይሆናል ያልኳቸውን ሶስት ነጥቦች አንስቼ ሃሳቤን ላጠቃል። አንደኛ በኔ እይታ ለኛ የሚሻለን በመድብለ-ዘውጌ ዴሞክራሲ (multi-ethnic democracy) ማዕቀፍ ሀገራዊ ብሄርተኝነትን ኮትኩቶ ማሳደግ ነው። በህንድ እና መሰል ሃገራት ተተግብሮ እንዳየነው መድብለ-ዘውጌ ዴሞክራሲ ሃገራዊ እና የዘውጌ ማንነቶችን ሚዛን ጠብቆ የመያዝ ብቃት አለው። የግለሰብ እና የቡድን መብቶችን አጣጥሞ ያስተናግዳል። መርሆው ተጓዳኝ እና ተደራቢ ማንነት ያላቸውን የተለያዩ የማህበረሰቡ አባላት በእኩል ዜግነት የሚያስተናግድ የፖለቲካ ስርዓት እዉን ማድረግ ነው። አካታችነቱ እንዳለ ሆኖ ስኬታማ መድብለ-ዘውጌ ዴሞክራሲ ለጋራ እሴቶች ግንባታ እና ጥበቃ ልዩ ትኩረት ይሰጣል። በስምምነት የሚፈጠር የጋራ እሴት ማዕከላዊ ይሆንና የዳርቻውን ማንነት  በአዝጋሚ ስበት ያስገባል። በሂደቱም በማንነት ላይ ሳይሆን መርህ ላይ የቆመ፣ የግለሰብና  የቡድን መብቶችን አማዝኖ የሚያስተናግድ  የዜግነት ፖለቲካ እዉን ይሆናል።
ሁለተኛ በዜግነት ፖለቲካ የተቃኘ መድብለ-ዘውጌ ዴሞክራሲ ለመገንባት ህገ-መንግስቱን ማሻሻል ቁርጠኝነት የሚጠይቅ አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ነው። ከማሻሻያው ሥራ በፊት ግን ሕዝባዊ ምክክር ያስፈልጋል። ልሂቃኑ  የሃሳብ መሪነቱን ድርሻ ይዘው አወዛጋቢ የሆኑት ጉዳዮች በስፋት ዉይይት ቢደረግባቸው ህዝቡ በእዉቀት ተመስርቶ ለማሻሻያው ድጋፍም ሆነ ተቃዉሞ ማድረግ ይችላል። ሁሉም ባለድርሻ አካልት (ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ምሁራን ወዘተ) ቁልፍ በሆኑ ህገ-መንግስታዊ ጉዳዮች ላይ ባደባባይ ሲሟገቱ  አስተፃምሮው (the synthesis) ለዉሳኔ የሚጠቅም አሳማኝና አስተማማኝ እዉቀት ይፈጥራል። የሀገርን ዘላቂ ጥቅም ለማስጠበቅ በእዉቀት ላይ ተመርኩዞ የሚሰራ ፖለቲካ አማራጭ የለውም።
በመጨረሻም በፖለቲካ መግለጫችን፣ ትንታኔችንና ዲስኩራችን የምንጠቀማቸው ቃላት እና ፅንሰ-ሃሳቦች ግልፅና አግባቢ መሆን ይኖርባቸዋል። ዓለም በቃል ይፈጠራል ነውና በትርጉም ካልተግባባን በተግባር መተላለፋችን የግድ ነው። ለምሳሌ ከላይ እንደጠቀስኩት ህገ-መንግስቱ ‘ብሔር፣ ብሔረሰብና ሕዝብ’ ብሎ የሚጠራቸው ስብስቦች በተጨባጭ እነማን እንደሆኑ ግልፅ አይደልም። ፅንሰ-ሃሳቡ ከነፍቹ ከዉጭ ተቀድቶ የገባ በመሆኑ ከኛ እውነታ ጋር አልገጠመም። ሌላም የተለመደና ችግር ያለበት አባባል አለ። ከተለያየ የዘውጌ ቡድኖች (ethnic groups) ብንወለድም ኢትዮጵያውያን ዘራችን አንድ ነው፣ ጥቁሮች ነን።  ስለዚህ በተለምዶ እንደሚባለው በሽታችን  ዘረኝነት ሳይሆን አክራሪ ዘውጌነት (ethnic extremism) ነው።  ችግራችንን በትክክለኛ ስሙ  መጥራት አንድ እርምጃ ወደ መፍትሔው ስለሚያቀርበን የፖለቲካ እና የፖሊሲ  ውይይታችን ለጠራ ሃሳብና አመንክዮ ትኩረት መስጠት አለበት።

Sunday, December 16, 2018

ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት እና የሠራተኛው መደብ አምባገነንነት ፅንስና በኢትዮጵያ ውስጥ ያስከተለው ሰቆቃ በነገሰ ጉተማ




                                                                                     መግቢያ
The TPLF.ይህ ፅሁፍ  ስለአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ምንነትና  አመጣጥ እንዲሁም  ባለፉት 40 ዓመታት በኢትዮጵያ ሕልውናና እድገት ላይ ያሳደረውን  የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የባህላዊ  ተጽእኖ  ይዳስሳል።  በማጠቃለያውም ተቃዋሚ  ፓርቲዎችና ዴሞክራሲያዊ  ድርጅቶች  ያለባቸውን  ታሪካዊ  ኃላፊነት በአንድነት እንዲወጡ ይጠይቃል። ጠለቅ ያለ ምርመራ ማድረግ ለሚፈልጉ በማጣቀሻዎች ሥር ያሰፈርኳቸውን  መፃሕፍትና ድረገጾች መመርመር ጠቃሚ ነው።
ካርል ማርክስ፣ ቭላድሚር ሌኒን እና የ”ሠራተኛው መደብ (ፕሮሌታሪያት)” አምባገነናዊ መንግሥት   አመሠራረት
በ1917 ዓ. ም.  እ.አ.አ. በቭላድሚር ሌኒን የሚመራው የሩሲያ ኮሚኒስት ፓርቲ (ቦልሼቪኮች) በጥቅምቱ አብዮት (ኦክቶበር ሬቮሉሽን) የሩሲያውን ዳግማዊ ኒኮላስን መንግሥት ከሥልጣን በማውረድ “የሠራተኛውን (ፕሮሌታርያት) መንግሥት” መሠረተ። ሶቪየት ሕብረትም ተፈጠረች። በጊዘው በቦልሼቪኮች የተመራው አብዮት“ሠራተኛውን መደብ ወይም ፕሮሌታሪያቱን” ሥልጣን ላይ ቢያመጣም የሩስያው ሠራተኛ (ፕሮሌታርያት)ብዛት፣ ጥንካሬና የንቃት ጥልቀት እንደሌሎቹ ካፒታሊዝም የጎለመሰበት የአውሮፓ ኡገሮች ሠራተኞች ስላልነበረ በሌኒን የሚመራው የሩሲያ ኮሚኒስት ፓርቲ  የሠራተኛው መደብ ፊታውራሪ (Vanguard of the proletariat) ሆኖ የሠራተኛውን ጥቅም እንዲያስጠብቅ ሞግዚት ሆኖ ራሱን ሾመ። ምንም እንኳን በ1840ዎቹ የሠራተኛውን አምባገነናዊነት ፅንሰ-ሀሳብ የቋጨው ካርል ማርክስ፣ ማንኛውም በሥልጣን ላይ ያለ መንግሥት አምባገነን ስለሚሆን ፕሮሌታርያቱም ሥልጣን ከያዘ የሠራተኛው አምባገነንነት (Proletariat Dictatorship) ይፈጥራል ብሎ ነበር። ሆኖም በሩስያው የጥቅምት 1917 አብዮት አምባገነንነቱ የፕሮሌታርያቱ መደብ መሆኑ ቀርቶ የፊታውራሪው  ሞግዚት የኮሚኒስት ፓርቲው  ተቆናጠጠ። ከአብዮቱ በፊት በኮሙኒስት ፓርቲ ምሥረታ ወቅት አንዱ ውይይት የነበረው ሩሲያ ገና ከፊውዳል ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ስላልተላቀቀችና ሩስያ ውስጥ ጠንካራና ብቁ ፕሮሌታርያት ባለመኖሩ ማርክሳዊ ርእዮተአለምን ሙሉ በሙሉ መተግበር አይቻልም በሚለው ሃሳብ ዙርያ ነበር።  የነሌኒን ውሳኔውም በሩሲያ ውስጥ በቅድሚያ የፕሮሌታሪያቱን አምባገነናዊ ሥርዓት በመመሥረት አብዮቱ በሁለት ደረጃዎች ተካሂዶ  ወደ ኮሚኒዝም መሸጋገር አለበት የሚል መርሆ ተከተሉ። ለዚህም የሚሆን የተለየ ድርጅት መመሥረት እንዳለበትና ይህም ድርጅት “የሠራተኛውና የጭሰኛው አብዮታዊ  ዴሞክራሲያዊ አምባገነንነት” እንዲሆን ተደነገገ። በዚህ ፅንሰ ሃሳብ፣ ፓርቲው በማዕከላዊ ቁጥጥር የጠነከረ እንዲሆንና አመራሩም በርዕዮተ አለሙ ባመኑ አብዮተኞች ብቻ እንዲሆን ተወሰነ። እነዚህም አብዮተኞች በዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ተደራጅተው መዋቅሮች ዘርግተው በገበሬውና በፋብሪካ ሰራተኞች ውስጥ ሰርገው  በመግባት ትግሉን ይመራሉ ብሎ በማሰብ ነበር። ይህም ሥርዓት የሠራተኛውን (ፕሮሌታሪያቱን) የሥልጣን በላይነት አስጠብቆ ወደኮሚኒስት ሥርዓት ለመሸጋገር ያዘጋጀዋል ተብሎ ታምኖበት ነበር። ሌኒንና የኮሚኒስት ፓርቲው ጨቅላው የሠራተኛው መደብ በተደራጁ የቀድሞው መንግሥትና ፀረ-አብዮተኞች (አድሃርያን) በቀላሉ ሊገለበጥ ይችላል የሚል ፍርሃት ነበራቸው።
ከምሥረታውም ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ዴሞክራሲን ለሁሉም ሕብረተሰብ ያለአድሎ ለመተግበር ሳይሆን በሥልጣን ላይ ላለው ድርጅት አምባገነናዊ አገዛዝን ለማመቻቸት ነው። በተጨማሪም በፓርቲው ውስጥም ሆነ በፓርቲው ሥር ባሉ ድርጅቶች ውስጥ ነጻ የሆነና የተለያዩ ወይም የሚቃረኗቸው ሐሳቦች መወያየት ፓርቲውን ይከፋፍለዋል የሚል እምነት ስለነበረ የፓርቲውን የበላይነት ለመጠበቅ ሲባል ተቃራኒ ሃሳቦችንና ተቃዋሚ አንጃዎችን አይፈቅዱም።
በዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት(አምባገነንነት) ሥር የፖሊቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የሚሊታሪ መዋቅሮች ተጠያቂነታቸው ለገዥው ፓርቲ ወይም መሪ ነው። በዚህ ሥርዓት ውስጥ የገዢ ፓርቲው ወይም መሪው እነዚህን መዋቅሮች የራሱን አምባገነንነት እና ህልውና ለማረጋገጥ እንደፈቀደው የማዘዝና በተቃወሙትም ላይ ሽብር መፍጠር  እንደተገቢና እንደመብቱ ይቆጥረዋል። ሌሎችንም በሥሩ የፈጠራቸውን መዋቅሮች እንደዚሁ ርእዮተ ዓለሙንና የፖለቲካ መስመሩን ለማስከበርና ተቃዋሚዎችን ለመጨቆን ይጠቀምባቸዋል። በእውነተኛ ዴሞክራሲ ላይ የተመሰረተ ሥርዓት የህዝቡን ሰብዓዊ መብቶች ልዑላዊነት ሲያረጋግጥ፣ የመደራጀት፣ የመሰብሰብ፣ ያለምንም ተፅዕኖ ሃሳብን መግለፅን፣ በፈለጉበት እንዲኖሩ፣ ተወካዮቻቸውን ያለመንግሥት ተፅዕኖ እንዲመርጡ ሲያከብርና ሲጠብቅ በማዕከላዊነት ላይ የተመሠረተው “ዴሞክራሲ” ደግሞ የገዢው መንግሥት ፍፁማዊ አገዛዝ ያስከብራል።
ቀዝቃዛው ጦርነት፣ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት እና  የቅኝ ሐገራት ነፃነት እንቅስቃሴ 
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ድምደማ በኋላ በሶቪየት ሕብረት የሚመሩ የሶሻሊስት ሐገሮች በአንድ ወገን፤ በአሜሪካ መሪነት የተሰማራው የምዕራቡ የካፒታሊስት ሐገሮች ደግሞ በሌላው ወገን በመሆን እስከ 1990ዎቹ  የቆየ የቀዝቃዛው ጦርነት (cold war)  ያካሄዱ ነበር። በዚህም ጦርነት ጊዜ ሶቪየት ሕብረት የምስራቅ ብሎክ (Eastern Bloc) ወይም የኮሚኒስት ብሎክ የሚባል ቡደን ፈጥረው የዴሞክራቲክ ሶሻሊዝም ንቅናቄዎችን ለማስፋፋትና ኮሚኒዝምን የዓለም ሥርዓት ለማድረግ (ስለዚህም ኢምፔሪያሊዝምን ለማጥፋት)  ራዕያቸውን ሲተገብሩ በአሜሪካ የሚመራው የካፒታሊስት ሐገሮች ቡድን ደግሞ የምዕራብ ብሎክ (Western Bloc) ተብሎ የሶቪዬት መስፋፋት ለመግታት ተሰልፈው ነበር። ሁለቱም ኃያላን ቡድኖች በዚሁ ጊዜ ዘመናዊ የጦር መሳርያ መገንቢያና ማከማቻ፤ የጦር ሰራዊታቸው  ማሰልጠኛና ማጠንከሪያ፤ የፕሮፓጋንዳና የስለላ ጦርነት ማካሄጃ አደረጉት። ሁለቱም ጎኖች ለሚደግፉት ሃገር ወይም ተዋጊ ግንባር ገንዘብ በመስጠትና መሳርያ በማስታጠቅ ጦርነታቸውን በወኪል ተዋጊዎች (Proxy Warriors) ማድረጉን መረጡ።
በዚሁ የቀዝቃዛ ጦርነት ወቅት ብዙዎች በቅኝ ግዛት ሥር የነበሩ የአፍሪካ፣ የእስያና የደቡብ አሜሪካ ሐገሮች የነፃነት ትግል ሲያካሂዱ ርዳታ ያገኙት ከሶቪዬት ሕብረት ነበርና ከነፃነት በኋላ ብዙዎቹም የሶቪየት ሕብረትን ፈለግ በመከተል አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሶሻሊዝም በመገንባት ላይ ተሰማሩ። አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሶሻሊዝም  የፖለቲካ ኃይል በጥቂቶች እጅ አከማችቶ በማዕከላዊነት ላይ የተመሰረተ አምባገነናዊ አገዛዝን አሰፈነ።   እነዚህም ሐገሮች ከአፍሪቃ አንጎላን፣ ዚምባብዌን፣ ሞዛምቢክን፣ ሳኦ ቶሜ ፕሪንሲፕ፣ ኮንጎ ብራዛቪል፣ ናሚቢያ፣ ጊኒ ቢሳዎና የመሳሰሉትን ሲጨምር፤ ከደቡብ አሜሪካ ኩባ፣ ኒካራጉዋ፣ ግሬናዳና የመሳሰሉት ሆነው፤ ከእስያ ደግሞ ኢንዶቻይና የመሳሰሉት ነበሩ። ቻይናም በኮሚኒስት ፓርቲው በኩል የሯሳን ማኦይስት ሞዴል መሥርታ እነኮሪያ፣ ቬትናም፣ አልባኒያና የመሳሰሉትን ከኋላዋ አስከተለች።
ከላይ ለማሳየት እንደሞከርኩት የዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትና የአብዮታዊ ዴሞክራሲ አፈጣጠር የአንድን ድርጅት የበላይነት ለማረጋገጥ ነው።
ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት በደርግ ዘመን
ኢትዮጵያ እንደሌሎቹ የአፍሪቃ ሐገሮች በቅኝ አገዛዝ ቀንበር ሥር ባትወድቅም ብዙ የአውሮፓ መንግሥታት ቅኝ ሊያደርጓት ብዙ ሞክረዋል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ጣሊያን ከሐገራችን ተባርሮ የመልሶ ግንባታው ሲጀመር የኢኮኖሚ አርዳታና የመከላከያ ኃሎቿን መገንቢያ ከምዕራብ ሐገሮች ስታገኝ ቆይታ ከ1966 አብዮት በኋላ ሥልጣን የተቆናጠጠው “ጊዜያዊ” ወታደራዊ መንግሥት በማርክሲዝም-ሌኒኒዝም ርዕዮተ ዓለም በመጠመቁ ከምዕራብ ፊቱን ወደሶቪዬት ሕብረት  አዞረ። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሁሉም የእርዳታና መሳርያ ምንጩ የምስራቁ ብሎክ ሆነ፣ አገዛዙም እንደዚሁ። ውጤቱም ሐገሪቷ በወታደርዊ አምባገነንነትና በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ማጥ ውስጥ ለ17 ዓመታት ማቀቀች። ይህም የ17 ዓመታት አባዜ ሐገሪቷን በሁሉም ዘርፍ አድክሟት ለሕወሐት ሰለባ ዳረጋት። የተገላቢጦሽ ደግሞ የሕወሐት አማካሪ፣ ደጋፊና መሳሪያ አቀባይ የምዕራቡ ብሎክ ሐገሮች፣ በተለይም አሜሪካ ሆነች። ከደደቢት ጀምረው አዲስ አበባ እስከገቡ ድረስ በአሜሪካው የስለላ ድርጅት እንክብካቤነት አድገው  የደቀቀች ኢትዮጵያን ወረሩ ።
አምባገነናዊ ማዕከልነት በሕወሐት-ኢሕአዴግ እጅ እያደረሰ ያለውን ሰቆቃ እያየን ነው። የሕወሐት-ኢሕአዴግ ስንኩል ሕገመንግሥትም በሕዝብ ፊት “ሕጋዊነትን” እንዲያገኝ ይህንኑ የአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ አምባገነንነት መሥርቶ ላለፉት 27 ዓመታት ሕዝቡን የመከፋፈያና የራሱን ሕይወት ማራዘሚያ አድርጎታል። በነዚህ ዓመታት የሠራተኛውም ሆነ የገበሬው መደብ ሥልጣን መያዝ ቀርቶ ስማቸውም አይጠቀስም። ለሰብዓዊ መብት ታጋዩ ፕሮፈሰር አለማየሁ ገብረማርያም ይህንኑ የሕወሐት አምባገነንነት “… a thugocracy privatelymanaged and operated for theexclusive benefit of bloodthirsty thugtators.” (6) ብሎ ሰይሞታል።
ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት :- የሕወሐት-ኢሕአዴግ ቆርጦ ቀጥል ሥርዓት
የሕወሐት-ኢሕአዴግም መንግሥት የዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትን አገዛዝ የሚደግፉትን መሾሚያ፣ የሚቃወሙትን  መደፍጠጫ፣ ሕዝቡን በዘርና በጎሳ መከፋፈያ መሳሪያ አድርጎታል። በሥሩም የተፈጠሩት የተለያዩ ድርጅቶች የሕወሐት-ኢሕአዴግ አምባገነናዊነት ምሰሶ ከመሆን ሌላ እውነተኛ ዴሞክራሲን የሚያሳድጉ ተቋሞች መሆን አይችሉም። ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊት ኢ-ዴምክራሲያዊ ስለሆነ የመድብለ ፓርቲንና ሁሉን የሕብረተሰብ ክፍሎች የያዘ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን በተግባር አይቀበልም። ሕግ አውጭው፣ ሕግ ተርጓሚውና ሕግ አስፈፃሚው አንድ ሲሆን የሚያገለግለውም በሥልጣን ላይ ያለውን ፓርቲ ነው። ሕጉንም የሕወሐት-ኢሕአዴግ መንግሥት አንዳመቸው ሲለውጠውና አዲስ ሕግም ሲደነግግ ነበር። በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እነዚህ ሦስት አውታሮች አብሮ መሥራት ብቻ ሳይሆን እርስበርስ በመቆጣጠር የአገሪቷን ሕጋዊ ጉዳዮች ያካሂዳሉ። በዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ሦስቱም አውታሮች እንደአሻንጉሊት ክሮች የሚስበው የሕወሐት-ኢሕአዴግ መንግሥት ነው። በተጨማሪም የተለያዩ የኢኮኖሚው አውታሮችን፣ ምክር ቤቱን፣ የደህንነት ጥበቃውን፣ የመከላከያ ሰራዊቱን እና የመሳሰሉትን ለራሱና ለደጋፊዎቹ ጥቅም ያውላል።
ዶክተር መረራ ጉዲና “የኢትዮጵያ የታሪክ ፈተናዎች እና የሚጋጩ ሕልሞች – የኢህአዴግ ቆርጦ ቀጥል ፖለቲካ” በተሰየመው መጽሐፋቸው ውስጥ የኢህአዴግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ የፈጠራቸውን (ያስከተላቸውን) ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታም ሆነ ለልማት ብልፅግና አንቅፋት የሆኑትን አሥር ነጥቦችን በትክክል አስፍረዋል። ከነዚህም ውስጥ አንዱ ነጥብ “… የኢህአዴጉ ‘አብዮታዊ ደሞክራሲ’ ከሁሉም በላይ መንግሥትንና የመንግሥት ተቋማትን የአንድ ፓርቲ የግል ሃብት የሚያደርግና የመንግሥት ተቋማት ዋና ሥራቸው መሪዎችን ሥልጣን ላይ ለማቆየትና በሕግ የሚታወቀውን መንግሥትን ተክቶ የሚሠራ መንግሥት መፍጠሩ ነው። የዚህ ሁሉ ችግሮች እናት ሁሉ….. ደግሞ ከኢህአዴግ ‘አብዮታዊ ዴሞክራሲ’ የሚመነጨው የአንድ ፓርቲ የበላይነት (hegemony) ሕልም ነው።”(1)
ሕወሐት ለራሱ አመቻችቶ የፈጠረውን ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊ አምባገነንነት የ1968ቱን ማኒፌስቶ እቅድ ከግብ ለማድረስ እየተጠቀመበት ነው። ኢትዮጵያን በዘር ከከፋፈሏትና የሕዝቡንም አንድነት ካዳከሙት የሕወሀት-ኢሕአዴግ ተግባሮች ጥቂቶቹን ከዚህ በታች ቀርፌ አቅርቤአለሁ።
አንደኛ – ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትን በመጠቀም እንደ ደቡብ አፍሪቃው አፓርታይድ ሥርዓት ሕዝቡን በጎሳ፤ በቋንቋ፤ በክልል ከፋፍለው በማዳከም፤ የጨቋኝና ተጨቋኝ ብሔሮች ግንኙነት ፈጥረው የሐገሪቷን አንድነት አቃወሱት። ይህም ሕወሐት የራሱን ክልል ለማልማትና ሌሎቹ፣ በተለይም አማራውና ኦሮሞው፣ ኦሮሞውና ሱማሌው፣ ደቡቦችም እርስበርስና ከጎረቤቶቻቸው ደም አንዲፋሰሱ በማድረግ ብዙ ችግሮችን ፈጥረዋል። በሕወሐት-ኢሕአዴግ የተፋፋመው የዘር ክፍፍል ለኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ ህመም መሆኑ እንደማይቀር አይጠረጠርም።
ሁለተኛ – የሥርዓቱን የብዝበዛና የሌብነት መርበብ ዘርግተው የሐገሪቷን ሐብት ለግላቸውና ለደጋፊዎቻቸው መበልፀጊያ አድርገው የኢትዮጵያን ሕዝብ በኢኮኖሚያዊ ገደል አፋፍ ተንጠልጥሎ እንዲሰቃይ አደረጉት። ያለገደብ አንዲያድጉና እንዲዘርፉ የተለቀቁት እንደ ሜቴክ፣ ኤፈርት፣ የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽንና የሌሎችም ትላልቅ ኩባንያዎች የዝርፊያ መናኸሪያዎች ሆነው የባለሥልጣናትን፣ የዘመዶቻቸውንና የአጎብዳጆቻቸውን የውስጥና የውጭ ባንኮች አካውንቶች አንዲሞሉና የቅምጥል ኑሮ እንዲኖሩ አድርገዋል።
ሦስተኛ – ከማዕከላዊ መንግሥት ውጭ ለመሥራት የሞከሩ፣ ሥርዓቱን በተቃወሙ፣  አረመኔያዊ ተግባራቸውን ለዓለም ለማጋለጥ የታገሉት ጦማሮችን፣  ዓይን ባወጣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሽብርተኝነት ወንጀል ሰብስበው በየእሥር ቤት ከተቱ፤ ገረፉ፤ ሰለቡ፤ አሰደዱ፤ ገደሉ። ይህንንም ግፍ ሲፈፅሙ በአስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጅና በፀረ-ሽብር ሕግ ጥላ ሥር ተደብቀው ነው። የሕወሐት ፀረ ሽብር ሕግ በ1967 ዓ. ም. ከታወጀው የደቡብ አፍሪቃው ፀረ ሽብር ሕግ ጋር ተመሳሳይ ነው። የፕሪቶሪያው ዘረኛ መንግሥት እነዊኒ ማንዴላንና ሌሎችንም አፓርታይድን የሚዋጉ አካሎች በዚህ ሕግ ተጠቅመው ነበር ሲያስሯቸው፣ ሲገርፏቸውና ሲገድሏቸው የነበረው።(2)
አራተኛ – ሕወሐት-ኢሕአዴግ በወታደራዊ ትጥቅ፣ በገንዘብ፣ በቁሳቁስና፣ በምክር ርዳታ ሰጥተው ለሥልጣን ያበቋቸውን የምዕራብ ሃገሮችን ለማስደሰት ሲሉ የነፃ ገበያን (free market) ከዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊ አምባገነንነት  ጋር አዳቅለው መላቅጡ የጠፋበት የኢኮኖሚ መዋቅር ፈጠሩ። በኢትዮጵያ ሁኔታ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነትን ከነፃ ገበያ ጋር ለማደባለቅ መሞከር አምባገነኖች ጡንቻ ለማጠንከርና ከላይ በተጠቀሱት የመንግሥት ሞኖፖሊዎች መበዝበዝን መርዳትና  ሌላውን የግል ነጋዴዎችን እንዳይንሰራፉ ለማድረግ ነው። ያልተገደበ ዴሞክራሲያዊ ነፃነት (የመናገር፣ የመሰብሰብ፣ እንደልብ የመንቀሳቀስና በንግድ ሥራ መሠማራት) በሌለበት ሁኔታ ከራሱ አምባገነናዊ ጥቅም ውጭ የማይፈቅድን ሥርዓት ነፃ ገበያን በተግባር ላይ ሊያውል አይችልም(1,5)።
አምስተኛ – የምርጫ ቦርዱን እንደራሳቸው መሳርያ በመጠቀም የምርጫ ውጤቶችን በማስለወጥ ሲሸነፉ በማጭበርበር አሸናፊ ሆኖ መቅረብ፤ የተቃዋሚ ፓርቲዎች አባላትን በማሰርና በመግደል እውነተኛና አድልዎ የሌለበት ምርጫ እንዳይካሄድ አድርገዋል። ይህም የማጭበርበሪያ የምርጫ ቦርድ በነሱ ቁጥጥር ሥር ሆኖ  የነሱ ዕድሜ ማርዘሚያ  አንጂ ገለልተኛና አድልዎ የሌለበት ምርጫን ለማስተግበር አልነበረም። በዶክተር መረራ አገላለጽ የምርጫው ቦርድ ለሕወሃት ሥልጣን ላይ መቆያ ከሆኑት ሁለት ምርኩዞች አንዱ ሆኖ ቆይቷል። ሁለተኛው ምርኩዝ የጠመንጃ አፈሙዝ ነው።
ስድስተኛ – በካድሬዎቻቸውና በስለላ መርበቦቻቸው በሰፈርና በቤተሰብ ውስጥ ጠልቀው በመግባትና ሕዝቡን ለረጅም ዘመናት ያስተሳሰረውን የባሕል “ድርና ማግ” በመበጣጠስ፤ የሕዝብን መሪዎች በተለያዩ ምክንያቶች በመወንጀል ከሥልጣን አውርደው የራሳቸውን ካድሬዎችና ታማኞች በመትከል፤ ሕዝቡ እርስ በርሱ እንዳይተማመንና በጥርጣሬና በፍርሃት እንዲጠላላ አድርገውታል። ይህ ዓይነቱ የከፋፍለህ ግዛ ተንኮልና የራሳቸውን ጎሳ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የባህል ቁልፍ ቁልፍ ቦታዎችን በመያዝ የበላይነትን እንዲያገኙ የማድረግና የሌላውን ሕዝብ በነዚሁ አውታሮች የበታች እንዲሆኑ በመጨቆን፣ ቀድሞ የነበረውን የሕብረተሰብ ክፍል በማባረር ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችን በመተካት ከፍተኛ የህብረተሰባዊ  ምህንድስና (ሶሻል ኢንጂነሪንግ) በማከናወን ላይ ተሰማርተዋል። በዘርና በብሄር ለይቶ ሰውን የበላይነትና የበታችነት  መፍጠር የባርያ ሥርዓት ባሕርይ ነው።
የለውጥ ጭላንጭል
ኢትዮጵያና ሕዝቧ ከ40 ዓመታት በላይ በፈጀ አምባገነናዊ አገዛዝ ሥር ተቆራምተው ብዙ መቶ ሺዎች ሕዝብ ካለቀ በኋላና ያንኑም ያህል በስደት ከተበታተነ በኋላ አሁን የለውጥ ጭላንጭል እየታየ ነው። ይህም የለውጥ ጭላንጭል ሊመጣ የቻለው የኢትዮጵያ ሕዝብ የረጅም ጊዜ ትግል  በተለይም ባለፉት ሶስት ዓመታት ወደማይመለስበት ደረጃ (critical juncture) ላይ በመድረሱና ምንም ዓይነት ጊዜያዊ አዋጅም ሆነ የጠመንጃ ጋጋታ ሊያቆመው አለመቻሉ ነው።  ይህም ሕዝባዊ አመጽ የገዢውን ፓርቲ ከመሠረቱ አናግቶት የጠቅላይ ሚንስቴር ኃይለማርያም ደሳለኝን በ”ፈቃደኝነት” ከሥልጣን  መውረድን አፋጥኖ የዶክተር አብይ አሕመድን  ወደሥልጣን መምጣት ጥርጊያ መንገድ ከፍቷል።
ክቡር ጠቅላይ ሚንስቴር ዶክተር አብይ አሕመድ ድርጅታቸው ቢወድም ባይወድም ያለፉትን የሕወሐት-ኢሕአዴግን አስከፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰትና የመንግሥት ሽብርተኝነት አምኖ በግልፅ ጥፋቱን በመቀበል ራስን የማነፅና ሥሕተቶችን የማረም ጉዞ ጀምሯል። ይህ ሂደት በራሱ የኢትዮጵያን ሁኔታ ልዩ ያደርገዋል። አንድ  አምባገነናዊ ገዢ ፓርቲ በምንም ዓይነት ሁኔታ ቀጥቅጦ ሲገዛው ለኖረው ሕዝብ እራሱን አጋልጦና ስህተቱን በግልፅ አምኖ ይቅርታ በመጠየቅና ለውጦች ለመተግበር የተነሳበት ሁኔታ በታሪክ ጥቂት ነው።
የክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ከሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ቢደገፍም ከራሱም ፓርቲ ውስጥ ተቃውሞ ደርሶበታል፤ በአደባባይ የግድያና የመፈንቅለ መንግሥት  ሙከራዎች ተደርገውበታል። ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ይህንን ለውጥ ከግቡ ለማድረስ እርምጃዎችን እየወሰደ ነው። እሱና ደጋፊዎቹ ለለውጡ መቆማቸውን በወሰዱት እርምጃዎች አሳይተዋል፤ እያሳዩም ናቸው። በግፍ የታሰሩ ተቃዋሚዎችንና የሚዲያ ሰዎችን ፈተዋል፤ ሰብዓዊ መብትን የጣሱና የኢትዮጵያን ሕዝብ ያሰቃዩትን ሰብስበው በሕግ ተጠያቂ ማድረግ ጀምረዋል፤ የካቢኔና የአመራር ለውጥም እያካሄዱ ነው። ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ድርጅቶች እንዲመለሱና የዴሞክራሲያዊ  ሥርዓት መመሥረቱ ላይ እንዲሳተፉ በሩን ከፍተዋል፤ የሐገሪቷን የመከላከያ ኃይልም ከአንድ ፓርቲ አገዛዝ ለማላቀቅ አየሠሩ ነው፤ በሌብነት ሐገሪቷን ያራቆቱትንም እያሳደዱ ነው። በዓለም አቀፍ ደረጃም ብዙ የሚያረኩ ድርጊቶችን አስመዝግበዋል።  ከ18 ዓመታት በላይ የፈጀውን የኤርትርያና የኢትዮጵያን ፍጥጫ ወደሰላም አድርሰዋል።
በተቃራኒውም ጥቅማቸው የተነካባቸው የገዢው ፓርቲ ተጠቃሚዎችና ደጋፊዎቻቸው አንዲሁም ከሐገሪቷ ውጭ ሆነው ሃገሪቷን ሊበታትኑ የሚፈልጉ ድርጅቶች ለውጡን ለመቀልበስ ሌት ተቀን እየጣሩ ናቸው። ፀረ-አንድነት ወሬዎችን በአስመሳይ ሶሻል ሚድያ በመዝራት፤ ገንዘብና ትጥቅ በመስጠት ሐገሩን በዘርና በቋንቋ ለያይተው ለማጋደል እየሠሩ ናቸው።  የሕወሐት አባላትና ሎሌዎቻቸውም የአብዮታዊ ዴሞክራሲና ሕገመንግስቱ ይከበር እያሉ እያለቀሱም ናቸው። በዚህም ለቅሷቸው ምን ለማለትና ለማድረግ እንደሚፈልጉ ማወቅ አያዳግትም።  ግምገማና ተሃድሶ! እያሉም ደጋግመው የሚጮሁ የሕወሐት ሰዎችም እስከዛሬ ድረስ በዚያው በግምገማና ተሃድሶ ሕዝቡን ሲያታልሉት ኖረው የሃገሪቷን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ሰብዓዊ መብቶችን ተሰምቶ ከማይታወቅበት አሳፋሪ ዝቅጠት ውስጥ ከተውታል። ከመጀመሪያው በተጣመመ መሠረት ላይ የተገነባውን መዋቅር ምንም ዓይነት ግምገማና ተሃድሶ ሊፈውሰው እንደማይችል ለማየት ተስኗቸዋል። እነሱ ግምገማና ተሃድሶ ባደረጉ ቁጥር የኢትዮጵያ ሕዝብ ሰቆቃ እየባሰበት እንጂ እየቀነሰለት አልሄደም። ለሕወሐት ደላሎችና ካድሬዎች ግምገማ እናድርግ ማለት “ጨቁነናችሁ አላበቃንምና ዘይቤያችንን አድሰን ለበለጠ ብዝበዛ እንድንመለስ ሌላ ዕድል ስጡን” ማለት ይመስላል።
መዘንጋት የሌለብን አብዮታዊ ዴሞክራሲ ወይም ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት አሁንም የሕወሀት-ኢሕአዴግ መንግሥት አምባገነናዊ የአገዛዝ ስልት ሆኖ እንዳለ ነው። የአሁኑም  አምባገነናዊ ሥርዓት በእውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መተካትና  ሕገመንግሥቱ ዴሞክራሲን እንዲደግፍ መሻሻል ወይም መለወጥ ይኖርበታል። ስለዚህም ይህን ለውጥ ወደፊት ማራመድና እውነተኛው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲፈጠር ተግቶ መሥራት  የሁላችንም ሃላፊነት ነው።
ይድረስ ለተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ድርጅቶች
ቁጥራችሁ የበዛ አገር አቀፍ እና ክልላዊ ፓርቲዎች ተደራጅታችሁ እንዲሁም ሌሎች ተቃዋሚ ድርጅቶች፤ በኢትዮጵያ ሕዝብ ትግል ተሳትፋችሁ የሕወሐት-ኢሕአዴግን መንግሥት ስትጋፈጡት  ቆይታችኋል። ለዚሁምበድርጅትም ሆነ በግለሰብአስከፊ ስቃይ ተቋቁማችሁ ለአገራችሁም ፍቅር ከፍተኛ ዋጋ ከፍላችኋል። በተቃራኒውም ሲታይ ልዩነቶቻችሁ የጠነከረ ድርጅት አንዳትፈጥሩና በሕብረት እንዳትታገሉ እንቅፋት ሆኖባችኋል። ይህም እውነታ ሕዝቡንም በመከፋፈል በጠነከረ አንድነት አንዳይታገል አድርጓል። ይህንንም ድክመት የሕወሐት-ኢሕአዴግ መንግሥት የራሱን ሥልጣን ላይ ማራዘሚያ አድርጎ ተጠቀሞበታል። አሁንም ልዩነታችሁን ወደጎን አስቀምጣችሁ ይህን  የለውጥ ዕድል ተጠቅማችሁ ጠንካራ ድርጅት በመመሥረት ለሐገራችን ዴሞክራሲያዊ  መንገድ መቀየስ ይኖርባችኋል። ይህንም ማድረግ ባትችሉና የኢትዮጵያን ሕዝብ እንደገና ለጭቆና ቀንበር አሳልፋችሁ ብትሰጡ ውርደቱ የናንተና የናንተ ብቻ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብም ይፋረዳችኋል። በዶክተር አብይና ረዳቶቹ በሩ ተከፍቷል። ለምን ጊዜ ያህል ተከፍቶ እንደሚቆይ የሚወሰነው በእናንተና በኢትዮጵያ  ሕዝብ ነው።  በምንም መንገድ የ97ቱም ሆነ የ2002ም ሆነ የ2007 የምርጫ ቀውሶች መደገም የለባቸውም። ከአሁን ወድያ የምርጫ ሳጥኖች ተስፋ በቆረጠ ሕዝብ “የስድብና የተበላሹ የምርጫ ወረቀቶች”(5)ተሞልተው ማሸነፍ የሌለበት ፓርቲ የሚያሸንፍበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ኢትዮጵያ ወደፊት የመራመድ እንጂ ወደኋላ የመመለስ ምርጫ የላትም።
ማጣቀሻዎች፡
  1. ዶክተር መረራ ጉዲናየኢትዮጲያታሪክና የሚጋጩ ህልሞችየኢህአዴግ ቆርጦ ቀጥል ፖለቲካ, 2008 እትመት
  2. Nelson Mandela – Long Walk to Freedom
  3. ኤርሚያስ ለገሠየመለስ ልቃቂት
  4. በተለያዩ አከባቢዎች ለሚቀሰቀሱግጭቶች ህወሓቶች እና አክቲቪስቶች ተጠያቂ ናቸው! Seyoum Teshome October 27, 2018 – https://ethiothinkthank.com/2018/10/27/the-role-of-tplf-elites-and-activists-in-inciting-ethnic-conflict/
  5. ሀብታሙ አያሌውከህወሓት ሰማይ ሥር, 3 እትም
  6. ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም – “The End of Thugtatorship and Rise of the Rule of Law in Ethiopia”. November 19, 2018.  https://ecadforum.com/2018/11/19/the-end-of-thugtatorship-and-rise-of-the-rule-of-law-in-ethiopia/
  7. Daren Acemoglu & James A. Robinson -Why Nations Fail –
  8. https://www.britannica.com/topic/democratic-centralism
  9. http://nazret.com/blog/index.php/2006/12/10/ethiopia_tplf_revolutionary_democracy
  10. https://www.opride.com/2017/12/29/ethiopia-eprdf-ditch-democratic-centralism-avoid-civil-war/
https://yefiyefitun.wordpress.com